Friday, December 26, 2014

ታህሳስ 28 1984 አ.ም. የገና ዕለት (Long day in Jimma)

ለኔና ለነ መንጌ መታወስ ያለበት ቀን ይህ ይመስለኛል:: የልጅነት ትዝታ.......

የገና ለት ጠዋት ስድስታችንም ማለትም እኔ : መንጌ: አምሳሉ: ሚሊዮን: አብይና ማስረሻ በአሉን ምክንያት በማድረግ ኪዳነምህረት ቤተክርስትያን በመሄድ ተሳልመን ወደ ጤና ሳይንሱ ግቢ ተመለስን:: ከዚያም ከቁርስ በሁዋላ ጠዋቱን በጅጤሳ መሰብሰቢያ አዳራሽ ውስጥ በተማሪዎች ተዘጋጅቶ በነበረው የፀሎትና መንፈሳዊ ትምህርት ፕሮግራም ላይ ተገኘን: ከአብይ በተቀር:: አዳራሹ  በእጣንና ዑድ ጭስና መአዛ ታውዶ ነበር:: ረዣዥም ሳር ፈንጠር ፈንጠር ብሎ በሰፊው አዳራሽ ውስጥ ተጎዝጉዙዋል:: በአዳራሹ አንድ ወገን እንደ መድረክ አይነት የተዘጋጀ ቦታ ይታያል:: መሃል ላይ የየሱስ ክርስቶስ ስዕል የታያል በግራና በቅኝ የሚበሩ ሻማዎች የተሸከሙ ቀንዲሎች አሉ:: ከመድረኩ ፊትለፊት ጀምሮ እስከአዳራሹ መሃል ድረስ ያሉት መቀመጫ ወንበሮች በተማሪ ና በመምህራን ታዳሚዎች ሞልተዋል:: ነጠላ የለበሱ ተማሪዎች አንገታቸውን ደፍተውና ድምፃቸውን ዝቅ አርገው ከወዲያ ወዲህ እየተራወጡ ታዳሚውን ያስተናግዳሉ.......

ስድስታችን ከሰዓት በሁዋላ ተበታትነን የዋልን ሲሆን እኔና አምሳሉ አንድ ላይ ነበርን:: ከተማ መሃል የምትኖር አንዲት የአምሳሉ ዘመድ የሆነች መምህርት ቤት ሂደን ጠላ እየጠጣን ስንጫወት ቆየን::

ምሽቱን ሁላችንም ወደጤና ሳይንሱ ግቢ ተመልሰን ተገናኘን:: ለቀናት ተቁዋርጦ የነበረው መብራት ስለተመለሰ ደስ ብሎን ነበር:: በዚህም የተነሳ ምሽቱን የዳንስ ምሽት ለማድረግ በመስማማት አባይን ጨምረንና ሰባት ሆነን ፊልተር ለመጠጣት ዘውትር በንዲህ አይነት ወቅት ጎራ ወደምንልበት ግሪን ሆቴል አመራን:: ሰዓቱ ከምሽቱ አንድ ሰዓት ይል ነበር:: ግሪን ሆቴል ወለሉ በሳር ጉዝጉዋዝ ተሸፍኖ አመትባል መሆኖኑን ይናገራል:: ደስ የሚል መንፈስ ነበረው:: በግሪን ሆቴል ቆይታችን አምስት ጠርሙስ ፊልተር ለሰባት ጠጣን:: ይህ ክፍፍል አናሳ ቢሆንም ሁላችንም ከሰአቱን በየፊናችን ጠጥተን ስለነበር እኔና መንጌ ይበቃል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰን ነበር:: ስለዚህም ሌሎቹም ላይ ተፅዕኖ በማድረግ ከዚያ በላይ እንዳንጠጣ ከለከልን:: ነገር ግን ከአባይ በስተቀር ሌሎቹ በኔና በመንጌ  ሃሳብ አልተስማሙም:: የሆነ ሆኖ ግሪን ሆቴል ፊልተር አለቀ ተባለ:: ስለዚህም ሁላችንም ቤቱን ለቀን ወጣን:: እኔ መንጌና አባይ ወደ ጤና ሳይንሱ ለመመለስ ስንሻ እነ አብይና አምሳሉ ደሞ ለጉዳይ የሆነ ሰው ጋ እንሄዳለን በሚል ሰበብ ተለዩን:: እኔ ሁላችንም ተመልሰን ዶርማችን ገብተን እንድንጨፍር በመፈለጌና ያም ስላልተሳካ ክፉኛ ተበሳጭቼ  ሞቅታዬም በርዶ ወደ ጅጤሳሳ ተመለስኩ::

መንጌና አባይም አብረውኝ የተመለሱ ሲሆን ዋይት ሃውስ ጋ ስንደርስ ተለያየን:: እኔ ወዲያውኑ ተስፋሁነኝ የተባለ ጉዋደኛየን አገኘሁትና ሻይ ለመጠጣት ተያይዘን ወደ ውጭ ወጣን:: ከተስፋሁነኝ ጋ ብዙ ተጫወትን:: ብስጭቴም ለቀቀኝ:: ሻይ ጠጥተን ስንመለስ ሰዓቱ ከምሽቱ ሶስት ሰዓት ሆኖ ነበር:: ምሽቱ መቼም በጠፍ ጨረቃ የታጀበና የማይበርድ ብሎም የምይሞቅ ደረቅ የታህሳስ ምሽት ነበር:: በዚያ ሰዓት ከነአብይ ና መንጌ ጋ መንገድ ላይ ተገናንኘን:: እነአብይን ሳያቸው ንዴቴ አገረሸ:: አይኔን አጉረጠረጥኩ:: እነሱ ደሞ ነገር ለማለዘብ እኔን ዋይት ሀውስ ፈልገው አጥተውኝ ከመንጌ ጋ ሆነው እንደገና እየፈለጉኝ ነበር:: ስላጡኝ ይበልጥ ተበሳጭተውብኛል ለካ...የነሱ ንዴት ከኔ እንደሚበልጥ ስለተገነዝብኩ ለዘብ አልኩና እንደውም ላግባባቸው ሞከርኩ:: ነገር ግን በዚያው ቅፅበት በተመሳሳይ አርዕስት አብይና መንጌ ለብቻቸው ባደረጉት ክርክር ኃይለኛ አለመግባባት ውስጥ ገቡ:: አብይ ክፉኛ አኮረፈ:: ስለዚህ ሁለቱን ማግባባት ላይ ያተኮረ እንቅስቃሴ አደረኩ:: የመንጌና የአብይን ጭቅጭቅ ቆሞ ሲከታተል የነበረው አምሳሉ በበኩሉ ሁኔታውን እንዳለ ጥሎ ለመሄድ ወሰነ:: ከብዙ ንግግሮችና የቃላት ምልልሶች በሁዋላ እንደገና እሱንም አግባብቼ ሁላችንም ወደ ዶርም 006 ተመለስን::

ሀሳባችን ቅድም ተነጋግረን የነበረውን ዶርም ውስጥ የመጨፈር ፕላን ለማሳካት ነበር:: ዶርም እንደደረስን አብይ ትናንትና አምጥቶት የነበረውን ቴፕ ሪኮርደር ከራሱ ሎከር ውስጥ ላወጣው ቁልፉን ከመንጌ ተረከብኩ:: ቴፕ ሪኮርደሩ ሌላ ዶርም ውስጥ ስለነበር አውጥቼው እስከምመለስ አብይና ማስረሻ ከዶርም 006 ተሰውረዋል:: አሁን ተስፋ በጣም ስለቆረጥኩ እዚያ የነበሩትን በሙሉ “በሉ ደህና እደሩ: ማንኛችን ጥፋተኛ እንደሆንን እግዜር ይወቀው: ሁላችንም ግን በሆዳችን ክፉ እንዳናስብ” ብዬ ተሰናብቼ ወጣሁ:: ትንሽ እንደሄድኩ አምሳሉ ከሁዋላዬ እየተከተለኝ መጥቶ “እባክህ ሳምሶን በቃ ተመለስና ወጥተን ሻይ እንጠጣ” አለኝ:: እኔም እሺ በማለት ከአምሳሉ: ከመንጌ ና ከሚልዮን ጋ ከዋይት ሃውስ ወዲያ በሚወሰደው መንገድ አርገን ወደ ጤና ሳይንሱ መውጫ በር አቅጣጫ ሄድን:: በመንገዳችን ላይ የተማሪዎች መሰብሰቢያ አዳራሽ ስንደርስ ከአዳራሹ ውስጥ ከፍተኛ የሙዚቃ ድምፅ ይሰማ ነበር:: “አሀ እዚህ ፓርቲ አለ ማለት ነው?” ብለን ወደ አዳራሹ በር ስንጠጋ አብይና ማስረሻን አገኘናቸው:: በወቅቱ የተዘጋውን ረዥም የአዳራሽ በር ለማስከፈት ከሚጥሩ ሌሎች ተማሪዎች ጋር ተቀላቅለው ነበር:: አብይና ማስረሻን ይዘን ሻይ ለመጠጣት በሚል ጅጤሳን ለቀን ወጣን:: እዚህ ጋ ቁጥራችን ልክ እንደጠዋቱ ስድስት ሆነ ማለት ነው:: ሁላችንም ሞቅታችን በርዶ ስለነበር ከሻይ ይልቅ ወንድማማቾች ቡና ቤት ሂደን መጠጥ ለመጠጣት ተስማማን:: እዚያም ለስለስ ያለ ጠጅ ጠጣን:: ጥቂት ዘና አልን ሁላችንም:: እኔ በበኩሌ ለስለስ ያለ ሞቅታ ተሰማኝ:: ያቺ ለስላሳ ሞቅታ ሳታልቅ ወደ ዶርማችን ተመለስን: ዶርም 006:: እንደደረስን ያን መከረኛ ቴፕ ሪኮርደር ከተቀመጠበት አውጥተን ዘፈን ከፈትን: ድምፁንም እስከ መጨረሻው ለቀቅነው:: ሁላችንም እጆቻችንንና እግሮቻችንን ማወራጨት ጀመርን: ዳንስ ማለት ነው:: አንዳድንድ የተኙ ተማሪዎች ወደውና በግዳቸው ተነሱ:: ቆጥ ላይ የወጡትም ወረዱ:: ሙዚቃ የሸተታቸው ከሌላ ዶርም መጡና ተቀላቀሉን:: ኩርፊያ ተረሳ:: የሚችለውም የማይችለውም ባለ በሌለ ኃይሉ ይድንስ ገባ:........................all night long....all night.....all night ...


ቀደም ብሎ ለነበረው አለመግባባት ሁላችንም እርስ በርስ ተወነጃጅለናል: ጥፋተኛንውን ግን እግዚአብሔር ነው የሚያውቀው:: አብይ ከማስረሻ በስተቀር ሁላችንንም ይወነጅላል: በተለይም መንጌን:: መንጌ ደሞ በመጀመሪያ አብይን ቀጥሎም እኔንና ሌሎቹን ይከሳል:: እኔ ደግሞ አራቱን ማለትም አብይን: ማስረሻን: ሚልዮንና: አምሳሉን ቁዋጥሬባቸው ነበር:: እነሱ ደሞ አራቱም በኔ ተበሳጭተዋል:: 

Wednesday, December 17, 2014

ታህሳስ ሃያዎች-አስራዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት አ.ም.
የፍረሽማን ማጠቃለያ ፈተና ሰሞን

ለፈተናችን ሶስት ቀን ሲቀረው አራት ትምህርቶች እንደኮሶ አስጠሉኝ: ፊዚክስ: ሶሺዮሎጂ: ፈርስት ኤይድ ኮሙኒቲ  ሄልዝ:: ለትምህርትና ለንባብ የነበረኝን እጅግም ያልጋለ ፍላጎት ይበልጥ በረዶ እንዲሆን ያደረጉት እንዚህ ትምህርቶችና መምህራኖቻቸው ይመስሉኛል: አቤት ስጠላቸው! እርግጠኛ ነኝ ትምህርቶቹን ልጠላ የቻልኩት በመምህራኑ አስጠሊታ አታካች እንዲሁም የተዝረከረከ የማስተማር ዘዴ የተነሳ ነው:: በተለይ ፊዚክስ መምህር.....

የተዋበ መስሎ በሞራል የተጀመረው የአንደኛ ዓመት የህክምና ትምህርት በመሃል በዘመቻ ምክንያት ተቁዋርጦ: በመጨረሻው ላይ የሄው እንጨት እንጨት ብሎ ሊጠናቀቅ ነው:: የአንደኛ ሴሚስተር ውጤቴ መልካም የነበረ ቢሆንም ለዚህኛው ፈተና ዳግም ብቻ ሳይሆን የበለጠም ፈራሁ: እወድቅ ይሆን ብዬ...የተማሪ ነገር 

ፈተናው በእንግሊዝኛና በካልኩለስ ተጀመረ:: አቤት ካልኩለስ መቼም ከባድ ነበር:: ሁሉም ተማሪ አማረረ:: እኔ በበኩሌ ከፈተናው ስወጣ ናላዬ ዞሮ ስለነበር በማግስቱ ጠዋት ለሚጠብቀኝ organic chemistry ፈተና ምንም አይነት የመጨረሻ ዝግጅት እንደማላደርግ እርግጠኛ ነበርኩ:: ሆኖም ግን organic chemistry ፈተና ያን ያህል አልከበደኝም ነበር:: organic chemistry በተፈተንበት ቀን ከሰዓት የወሰድናቸው first aid  community health ፈተኖችም ደህና ነበሩ::

በእውነቱ እዚህ ወቅት ላይ ቆም ብዬ በእርግጠኝነት መናገር የምፈልገው ወደ ሁለተኛ ዓመት እንደማልፍ ነው:: በዚህ ምንም ስጋት የለኝም:: ነገር ግን አጠቃላይ ውጤቴ በአንደኛ ሴሚስተር ከነበረው በጣም ዝቅ ያለ ሊሆን ይችላል:: ለነገሩ ምን አገባኝ ካለፍኩ...

organic chemistry ፈተና በወሰድንበት ቀን ማግስት biology ፈተና ይጠብቀኝ የነበረ ቢሆንም እኔ ምሽቱን ያሳለፍኩት በቴሌቪዥን መመልከቻው አዳራሽ ውስጥ ነበር: relax እያደረኩ::

በተከታዮቹ ቀናት የቀሩትን ትምህርት አይነቶች በሙሉ ተፈተንናቸው:: 

የገና  ዋዜማ ፩፱፰፬ ..

የአንደኛ ዓመት ማጠቃለያ ፈተናችንን ተከትሎ የገና በዓል ታህሳስ ሃያ ስምንት ቀን ተከበረ:: ለወትሮው ሃያዘጠኝ የሚከበር ቢሆንም የዘንድሮው ሃያዘጠኝ ረቡዕ ማለትም የፆም ቀን ላይ ስለዋለ ነው መሰለኝ ከፊቱ ባለው የፍስክ ቀን እንዲከበር ሆነ:: የሆነ ሆኖ በዛሬው በዓል የሚደሰቱ ከሆን ደስ ሊላቸው የሚችሉት ለሃይማኖታቸው ያደሩ ጴንጤ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ብቻ ይመስሉኛል:: ምክንያቱም ካለፈው አርብ ጀምሮ ዛሬ አምስተኛ ቀን መሆኑ ነው: በጅማ ከተማ የኤሌትሪክ ኃይል ተቁዋርጡዋል:: መብራት የለም:: በዚህም ምክንያት ለማክሰኞ ዋዜማ ሰኞ ምሽት ሊደረጉ ታስበው የነበሩ የመዝናኝና የሙዚቃ ምሽቶች ሳይካሄዱ ቀሩ:: እኔና ጉዋደኞቼም አብይ ተውሶ ባመጣው ቴፕ ረኮርደር ዶርማችን ውስጥ ሙዚቃ እየሰማን ለመጨፈር አቅደን ነበር:: ምን ዋጋ አለው...አልሆነም:: ለነገሩ እነ መንጌ: አብይ: አምሳሉ: ማስረሻ ሚሊዮን ወደ ግሪን ሆቴል ሄደው ጠጣ ጠጣ አድርገው ተመለሱ:: እኔ ያልጠጣሁ ቢሆንም የዋዜማውን ምሽት አብሬያቸው ዋይት ሃውስ በሚገኘው ዶርም 006 ስጫወትና ስዘፍን አመሸሁ:: ዶርሜ ባይሆም እዚያው አደርኩ:: የዶርሙን ጨለማ በገፈፈች አንዲት ሸንቃጣ ሻማ ታግዘን የእንግሊዝኛና የአማርኛ ዘፈኖች እራሳችን እየዘፈንን ዶርሙንም ሆነ አጎራባች ዶርሞችን በጠበጥናቸው:: በተለይ መንጌ አይረሳኝም: ከዚያ ቀን በፊት አሳይቶት በማይውቅ ሁኔታ ይደንስና ይጫወት ነበር……ትዝታ

Thursday, December 11, 2014

ህዳር መጨረሻ ገደማ አስራ ዘጠኝመቶ ሰማንያ አራት ..
ካባለፈው የአውቶቡስ ተራ አጋጣሚ በሁዋላ በተሰማኝ ድንጋጤ ስርዓት ይዤ ትምህርቴን የምቀጥል መስሎኝ የነበረ ቢሆንም ፈፅሞ በጥናት ልተጋ አልቻልኩም:: ከፍተኛ የሆነና ስር የሰደደ የጥናት ፍላጎት ማጣት ውስጥ ገባሁ:: መማር ራሱ አዙሪት ነገር ሆነብኝ:: አለርጂክ! ይህን ከመረዳት የመነጨ ጭንቀት በአምሮዬ በየቀኑ ይመላለስ ገባ:: ቤተ ክርስትያን መሄድ: መፅሐፍ ቅዱስ ማንበብ እንዲሁም ማስታወሻ መፃፍ ጭንቀቴን የሚያቃልል አልሆነም:: የሚገርመው ግን ቀስ በቀስ ጭንቀቱን ለመድኩት:: ከዚያማ የሚያስጨንቀው አለመጨነቅ ሆነ…….ይገርማል

ወደቤት መመለሻዬ ተቃርቡዋል:: የሁለተኛ ሴሚስተር ፈተና ከጥቂት ሳምንታት በሁዋላ ተፈትነን አመቱን እናጠናቅቃለን:: የቤተሰቤን ሁኔታ ለጊዜው አላውቅም:: መልክትም ሆነ የኪስ ገንዘብ ከተላከልኝ ሰነበተ:: ነገር ግን እግዜር ይመስገን: ቢያንስ አባቴ ከእስር ቤት ተፈትቱዋል::

ከምሽቱ አራት ሰዓት በሁዋላ ለጥናት መቆየት ስላቃተኝ ሌሊት ሌሊት አስር ሰዓት ላይ እየተነሳሁ ማንበብ ጀምሪያለሁ:: እየሰራ ያለ ፕላን ይመስላል:: ይህ የጠዋት ሰዓት አእምሮዬ የመጨረሻ ብሩህ ደረጃ ላይ የሚሆንበት ሰዓት መሆኑን ከተገነዘብኩ ውዬ አድሬያለሁ:: እናም ሰሞኑን በዚህ ሰዓት የማነበው ከባዱና ዘግኛኙን Organic Chemistry ነው:: Sociology የሚባለውን ትምህርት አለማንበብ ብቻ ሳይሆን ክፍል ገብቼ የሚሰጠውን ሌክቸር እንኩዋን መከታተል ትቻለሁ:: 



ታህሳስ ስድስት አስራ ዘጠኝመቶ ሰማንያ አራት ..

መልካም ዜና:: አባቴ የማስተማሩን ሥራ እንደገና መጀመሩን በቅርቡ ለእረፍት ወደ አዲስ አበባ ሂዶ የተመለሰው የሰፍሬ ልጅ ታጠቅ ነገረኝ:: እህቶቼና ወንድሜም ትምህርታቸውን በሰላም እየተከታተሉ መሆኑን ተረዳሁ:: ታጠቅ እረፍት ላይ ሳለ ወደኔ ቤተሰቦች ቤት ብቅ ብሎ ነበር:: ወደ እረፍቱ ሲሄድ እኔ የፃፍኩትን ደብዳቤ አድርሶ ከነሱ ደግሞ ደብዳቤ: ጥቂት ገንዘብ: ዳቦ ቆሎና ሳሙና ይዞ ተመለሰ:: የቤተሰቡ አባላት: የመጨረሻዋ እህቴን ጨምሮ ደብዳቤ ፅፈው ልከዋል::ቤተሰቤ በደህና ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ በማወቄ በእውነት በጣም ደስ አለኝ:: ቀለለኝም:: በዚህ ቀን ለሁለተኛው ሴሚስተር ማጠቃለያ ፈተናችን የቀረው ሁለት ሳምንት ብቻ ነው:: ጥናት ተጧጧፏል:: ከባዮሎጂ Genetics: Plant Physiology: ከሂሳብ The Theories of Calculus: ከፊዚክስ Thermodynamics: Relativity ፈተና ውስጥ በዋነኝነት እንደሚካተቱ ተነግሮናል:: ብዙ ተማሪዎች ሳይተኙ እስከ ሌሊቱ ስምንት ሰዓት እንደሚቆዩ ለማየት ባልታደልም ሰምቻለሁ:: እኔ ይህችን አጭር ማስታወሻ ፅፌ ለመትኛት ስዘጋጅ ሰዓቱ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ከሃምሳ ዘጠኝ ደቂቃ ይላል…..

Saturday, November 22, 2014

ሁለተኛ ግንዛቤ

ህዳር ቀን ፩፱፰፬ ..

ሁለተኛ ግንዛቤ

ባለፉት ቀናት የሚድ ሴሚስተር ፈተና ውጤቶቻችንን አወቅን:: በኔ በኩል ከሂሳብ በስተቀር ውጤቶቼ በሙሉ ደካማ ነበሩ:: የጠበኩት ቢሆንም እውነት ሆኖ ሳየው ደነገጥኩ:: ብዙ ሌሎች ተማሪዎች በልጠውኛል:: ከሐይ ስኩል; በሁዋላ እንዲህ አይነት ሁኔታ ሲያጋጥመኝ የመጀመሪያው ነበር: ማለቴ በትምህርት በሌሎች ብዙ ተማሪዎች መበለጥ::መንፈሴ ሲጎዳ ተሰማኝ:: ሂሳብ ሃምሳ ጥያቄ አርባ ስድስቱን በትክክል በመመለስ የኔ ውጤት ከፍተኛው ሳይሆን አይቀርም::  ሂሳብ መምህራችን ተስፋ ልደት ቢሮው አስጠርቶ “አንቺ ኮ አንበሳ ነሽ” ሲለኝ ማመን አልቻልኩም:: ምን ዋጋ አለው በሌሎቹ ውጤቶች የተጎዳውን ስሜቴን ሊጠግነው አልቻለም:: የጠቅላላ ፈተና ዉጤቴን ካወኩ በሁዋላ ድብርት በተከተሉት ቀናት እየተጫጫነኝ መጣ:: ለማንበብም ሆነ ለመፃፍ ያለኝ ሞራል ከበፊቱ የበለጠ ዝቅ አለ:: አንዳንዶቹን መምህራን ማየት ሁሉ አስጠላኝ:: ትንሽም ቢሆን ላቦራቶሪ ስንሄድ ይሻለኛል:: ምናልባት ላቦራቶሪ ውስጥ ከንባብ ከማዳመጥ ይልቅ ድርጊት ስለሚበዛ ይሆናል:: ሆኖም የያዘኝ ድብርት እየጠነከረ መጥቶ ለምንም ነገር ዝግጁ አለመሆን ደረጃ ላይ ደረስኩ::

ዛሬ አንድ ሃሳብ መጣልኝ:: ቤተሰብ ጋር ለጥቂት ቀናት ቆይቼ ለመመለስ አሰብኩ:: በእውነቱ የቤተሰብ ናፍቆት የለብኝብም ግን ከዚህ አካባቢ ለሁለት ለሶስት ቀንም ቢሆን መራቅ ድብርቴን ያሽለው ይሆናል ብዬ አሰብኩ::ይህን እፁብ ድንቅ የሆነ ሃሳብ ለማመንጨት በመቻሌ ራሴን ከፍ ከፍ አደረኩት:: ስር ከሰደደ ችግር የተወለደ ሃሳብ:: ችግሩ ግን ሃባ ሳንቲም በኪሴ የለም:: የቤተሰባችን ሁኔታ ባለፈው እንደገለፅኩት ምናልባትም ከኔ የባሰ ስለነበር ባሁኑ ሰዓትገንዘብ አይልኩልኝም:: ከተጨማሪ ማሰብ ወደተግባርም ከመሰማራት በሁዋላ ገንዘብ የሚያበድረኝ ሰው አገኘሁ-አባይነህ! ዛሬ ከሰዓት አውቶቡስ ተራ ትኬት ለማስቆረጥ: እሄዳለሁ:: ከቀናኝና ከተገኘ ነገ ለመሄድ ማለት ነው:: ለቤተሰብ እመጣለሁ ብዬ አልተናገርኩም:: እንደምሄድ ከአበዳሪዬ አባይነህና ከሰፈሬ ልጅ ታጠቅ በስተቀር ማንም አያውቅም:: እቤት ድንገት ከተፍ ስል ቤተሰብ ምን ይል ይሆን ብዬ አሰብኩ: ያው ይደነግጣሉ:: የተባረርኩ ሊመስላቸው ይችላል:: ይህን እንደሚያስቡ ሳስብ አንገቴን አመመኝ::

ከሰዓት በሁዋላ .........
ጅማ አውቶቡስ ተራ ደረስኩ:: በእውነቱ እዚህ አካባቢ ተገኝቼ የማውቀው ከዚህ በፊት አራት ግዜያት ብቻ ነው:: እነሱም ለመጀመሪያ ግዜ ስመጣ: ዓመቱ አጋማሽ ላይ ለእረፍት ስሄድና ስመጣ እንዲሁም ከሁለት ወራት በፊት ትምህርት ለመቀጠል ስመጣ ናቸው:: ሁሌም ቢሆን አውቶቡስ ተራ ውስጥ ብዙም የመቆየትና ቦታውን የማስተዋል ዕድል አጋጥሞኝ አያውቅም:: በዚያ ላይ ከዚህ በፊት ስሄድም ሆነ ስመጣ ከጉዋደኞቼ ከሌሎች ተማሪዎች ስለነበር በራሳችን ጨዋታ ተመስጠን አውቶቡስ ተራውን አናስተውለውም ነበር:: ዛሬ ግን ብቻዬን በግላጭ ተገኝቼ በጠራራ ፀሐይ አስተዋልኩት- አውቶቡስ ተራውን:: እውነትም በጣም ተራ ነው... ተራ ሰው ይርመሰመሳል...ተራ አውቶቡሶች ራስ የሚያዞሩ ጭሶቻቸውን እያቡለቀለቁ ይወጣሉ ይገባሉ:: ዕቃ ጫኝ ቀን በሎች አውቶቡሶቹ ላይ ዕቃ ይጭናሉ ያወርዳሉም:: በዚያ ራስ በሚመታ ፀሐይ ላባቸው እየተንተፈጠፈ ወዲያ ወዲህ ይራወጣሉ:: ብቻ በለት ተለት ኑሮዬ የማላየው አይነት ግርግር አየሁ:: ለምን እንደሆነ ባላውቅም በድንገት ፍርሃት ፍርሃት አለኝ:: በአንድ ግዜ ብዙ ሃሳብ በአምሮዬ በተዘበራረቀ ሁኔታ ተመላለሰ:: ሃይ ስኩልን አስታወስኩ:: ሰፈራችን ውስጥ ትምህርታቸውን የሙጥኝ ብለው ሲከታተሉ ከነበሩ በጣም ጥቂት ልጆች ውስጥ አንዱ እንደነበርኩ አስታወስኩ:: የማትሪክ ፈተና ተሳክቶልኝ ወደፊት እንድራመድም ሌተ ቀን ስፅልይ እንደነበር ታወሰኝ:: የማትሪክ ፈተና ውጤት ተለቁዋል የሚል ወሬ በስማበለው ሰምቼ ከኮልፌ ትምህርት ቤቴ እስከሚገኝበት አዲስ ከተማ ድረስ ከጉዋደኞቼ ጋር በሩጫ የገሰገስነው ባይኔ መጣብኝ:: ሁሉ እንግዲህ እዚህ አሁን ያለሁበት ደረጃ ላይ ለመድረስም አልነበር? አሁን ያለሁበትን ደረጃ ግን በሚገባ መርገጥ እየቻልኩ በቸልተኘነት በትክክል ባለመርገጤ አንገዳገደኝ....አውቶቡስ ተራውን እንደገና በአይኔ ሙሉ አማተርኩት:: ከቀን በሎቹ በተጨማሪ የለበሱት የነተበና ብዙ ከመለበስ የተነሳ የቆሸሸ ወንዶች ልጆች ግማሾቹ ተቀምጠው ግማሾቹም ቆመው ሲንቀሳቀሱ ተመለከትኩ:: ግ ይዘው የተጋደሙም አሉ:: ቤት የሌላቸው በረንዳ የሚያድሩ እንደሚሆኑ አልተጠራጠርኩም.......እኔ እንግዲህ ደበረኝ ብዬ ወደቤት ለመሄድ የአውቶቡስ ትኬት ለማስቆረጥ እዚህ ቦታ ላይ ተገኝቻለሁ... በዚያው ቅፅበት ወደ ጤና ሳይንሱ ግቢ በፍጥነት መመለስ አማረኝ:: ጤና ሳይንሱ እንዳለ አሰኘኝ:: አውቶቡስ ተራው በር እላዬ ላይ የሚዘጋብኝ ይመስልስል እዚያ መቆየት አልፈለኩም:: በሩጫ መውጣት ፈለኩ:: ወደቤት ለመሄድ በማሰቤም ሆን በመገፋፋቴ ፀፀት ብጤ ዳሰሰኝ:: በውይይት ታክሲ ወደ ጤና ሳይንሱ ሸመጠጥኩ:: በምሽቱ ሳይኮሎጂ መምህራችን ፩፪ ሰዓት ተኩል ጀምሮ ለሁለት ሰዓት ተኩል ያህል የሰጠውን ሌክቸር በጥሞናና ባፍቅሮት እንዲሁም በአክብሮት ተከታተልኩ........

Thursday, November 13, 2014

ሚድ ሴሚስተርና የአብይ ማስታወሻ


ጥቅምት ሃያ ሁለት አስራዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት አ.ም.

ሚድ ሴሚስተርና የአብይ ማስታወሻ
ከጥቅምት 18 እስከ 22 ባሉት ቀናት ውስጥ የ ግማሽ ሴሚስተር ፈተናዎቻችንን ወሰድን:: በእንግሊዝኛ ተጀምሮ : በኦርጋኒክ ኬሚስትሪ: ሳይኮሎጂ: ሶሺዮሎጂ :ፊዚክስ ና ማትስ ተከትሎ በ ባዮሎጂ ተጠናቀቀ:: እንግሊዝኛና ኦርጋኒክ ኬሚስትሪ ሁለቱም ከብደውኝ የነበረ ሲሆን: ሳይኮሎጂ ደግሞ ስለምወደውና በደንብ ስላነበብኩም ነው መሰል ቀሎኝ ነበር:: ፊዚክስ የጠበኩትን ያህል አልከበደኝም:: ሶሺዮሎጂ ግን የማልወደው ትምህርት ከመሆኑም ሌላ ፈተናውንም በሚገባ እንደማልወጣው አስቀድሜ ስለደመደምኩ ግዜ ሳላባክን በፍጥነት ነው ከፈተናው ከፍል የወጣሁት:: ጉዋደኞቼ ሳይገርማቸው አይቀርም::  በነገራችን ላይ በሚድ ሴሚስተር ፈተና ቀናት መሃል አንድ ምሽት የአንደኛ ሴሚስተር ውጤት ወረቀቴን ባጋጣሚ መፃሕፍ ቅዱሴን ስገልጥ አየሁት:: በጣም ማስደሰት ብቻ ሳይሆን ልክ የሌላ ሰው የሆነ ያህል አስቀናኝ:: እንደገና ደግሜ እንደማላመጣው ተሰምቶኝ ይሆናል:: 3.84 ይላል አጠቃላይ ነጥቡ.....ባጠቃላይ ስለ ሚድ ሴሚስተር ፈተና ጥሩ ስሜት አልተሰማኝም:: በደንብ አልሰራሁም:: ቢሆንም ባይሆን ብዬ ለዋናው የሴሚስተር ፈተና በርትቼ ለማጥናት በሚስጥር ለራሴ ቃል ገባሁ:: 

ባዮሎጂ ፈተናችንን የወሰድን እለት ከ ቀርብ ጉዋደኞቼ አንዱ የሆነው አብይ በጠየኩት መሰረት አጀንዳዬ ላይ የሚከተለውን ፅሁፍ አሰፈረ..


መጀመሪያ ብዕሬን በግል ማስታወሻህ ላይ እንድፈትን ዕድል ስለተሰጠኝ በጣም እግዜር ይስጥልኝ:: ስዎች ከራሳቸው አፍልቀው በሚፅፉት ከገፆች አልፈው ወደ መፅሐፍት ሲሸጋገሩ መስማት እጅግ በጣም ያስደንቀኛል::  በእውነቱ
እኔ እቺን ገፅ እንኩዋን ለመሙላት በጣም ነው የማንገራግረው::

ራሴን ሳላስተዋውቅ: ብዙ ያወራሁ መሰለኝ:: አብይ ሕሩይ እባላለሁ:: ትውልዴ አዲስ አበባ ከፍተኛ 11 ቀበሌ 02 በተለምዶ ስሙ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ነው:: ጅማን መዋያ ማደሪያዬ ያደረኩት የካቲት 12 ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤትን ወክለው ወደ ጅጤሳ ከመጡት “the magnificent three” ጋር ከመስከረም ፩፮ ፩፱፰፫ ጀምሮ ነው::

ስለራሴ ይህን ካስተዋወኩዋችሁ ዘንዳ አሁን ሰዓቱ ከምሽቱ ፮ መሆኑን ልንግራችሁ እወዳለሁ:: ዛሬ ፍፁም ነፃነት ተሰምቶኝ ነው የዋልኩት:: የ mid-semester ፈተናዎች ማሳረጊያ የሆነው ባዮሎጂን ጨርሰን በምሽቱ የቪዲዮ ትርኢት Police Academy የተባለውን አዝናኝ ፊልም ስመለከት ነው ያመሸሁት:: በእውነቱ ከሆነ ከፊልም አፍቃሪዎች መሃከል አንዱ ነኝ:: አላዘውትር እንጂ ፈተና በደረሰበት ሰሞን እንኩዋን ገብቼ ማየት የፊልም ፍላጎቴን ያረካልኛል:: የዛሬውን ምሽት show ለየት ያደረገው በቪዲዮ ማሳያው አዳራሽ በኩል ሲያልፉ እንኩዋን የሚሰቀጥጣቸው ሴቶች እህቶቻችን ሁለት ወንበር ለመጋራት መብቃታቸው ነው::


ነገ እሁድ ነው:: ጥሩ መደበሪያ ቦታ እንደሚያስፈልገኝ በማውጠንጠን ላይ ነኝ:: እንዲያውም አንድ በጣም የልብ ጉዋደኛዬ የሆነ ከአዲስ አበባ የመጣ ወዳጄን ጅጤሳን የማስጎብኘት ሃሳቡ መጥቶልኛል:: በዚሁ እሰናበታለሁ::

Sunday, November 9, 2014

ፈገግታ

በብሩህ አይኖች እይታ 
በአእምሮ ትእዛዝ ይሁንታ 
በጥርስ ድምቀት ሰጭነት 
በጉንጭ ቅላት ፍካት 
በከንፈር ስፋት ጥበት 
በዉፍረትና በቅጥነት
በአይን ዳርቻ መሸብሸብ
ገፅ በደስታ ሲከበብ 
ለተመልካች እይታ መስህብ 
እንደአበባ መአዛ: እንደ አበባ  ልዩ ሽታ 
እንደነፋስ ሽውታ: እንደፀሃይ ብልጭታ 
ፈገግታ!

ክፉን ከደግ: ሴትን ከወንድ 
ጨዋን ከሌባ: ጤነኛን ከእብድ
የረጋውን ከችኩል: አመለቢሱን ካመለኛው
ኡ ኡ ባዩን ከቀማኛው ከዘራፊው 
'ምታግባባ በአንዲት ቅፅበት እይታ 
ለልብ ለጋሽ እርጋታ...
ፈገግታ!

ሰውን የማክበር ምልክቱ: የባልንጀርነት ስሜቱ
የመውደድ ማፍቀር ማስረጃው: የታማኝነት መግለጫው
የንፁህ ልቦና ምስክሩ: የአዲስ ፍቅር ጅምሩ
የወዳጅነት መለያው: የሂወት ምግብ ማጣፈጫው
ፈገግታ...እንደአበባ ልዩ ሽታ: እንደነፋስ ሽውታ 
ለህሊና ሰጭ እርካታ: ከልብ ደራሽ ባንዳፍታ 
የደስታ ምንጭ ያላት መስህብ
ፈገግታ የሂወት ምግብ
ፈገግታ!

በር ይከፈት በፈገግታ 
ለእንግዳ ረዥም ቆይታ 
ለመስተንግዶው ድምቀት ማማር
ለእንግዳ ምቾት ለመፍጠር
ከምግብ መጠጥ በፊት ለማስታወሻ ለትዝታ
ይቅረብ ከልብ እንደልብ : ያልተሰሰተ ፈገግታ 
ፈገግታ!

ሰላም እንደምን አለህ: ሰላም እንደምን አለሽ 
እንደምን አሉልኝ አብዬ: ደህና ውለዋል እማምዬ
እንደምንድኖት ጌታዬ
ሰላም ዋላችሁ ጉዋደኞቼ
በጣም ደህና ነኝ ቤቶቼ
ባልንበት ሁሉ ለሰላምታ 
ይቅደመን ከልብ ፈገግታ!
ፈገግታ!

እግዜር ይስጥልኝ: ጌታ ይባርክህ
ብዙ ያኑርህ ያሳድግህ 
አመስግናለሁ አባትዬ 
መርቄሻለሁ እህትዬ 
ለተቀባይ ዋጋ የለው
ፈገግታዎ ከተለየው 
ለፈገግታ ይኑሩ: በፈገግታም ይናገሩ
መከራ ፊትዎን ይሰውሩ 

ፈገግታ...


መጋቢት 1982 አ.ም. የተፃፈ - በ ሳምሶን ኃይሌ:: ሃሳቡ እንዳለ ቢሆንም ያፃፃፍ ለውጥ ተደርጎበታል:: ከመጀመሪያው ግጥም የሄኛው በመጠን ያንሳል:: የመጀመሪያው ግጥም  ግንቦት 1982 አ.ም. በአዲስ ከተማ  ትምህርት ቤት በተደረገ  የተማሪዎች የግጥም ውድድር ላይ ቀርቦ ሶስተኛ ደረጃ ያገኘ ሲሆን በወቅቱ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቡዋል::

Wednesday, October 29, 2014

አሁንም የቀጠለ

አሁንም የቀጠለ

ይህ እንግዲህ የህክምና ትምህርት ቤት ወግ ስለሆነ አንዳንድ አንባብያንን እንዳያሰለች ስጋት አለኝ:: ነገር ግን ምንም ማድረግ አልችልም::

ጥቅምት አስራ አንድ አስራ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት አ.ም.
ባለፈው ተሳክቶልኝ ላይብረሪ ውስጥ ለሶስት ሰዓት ያለማቁዋረጥ ተቀመጥኩ:: እስከአሁን ድረስ እየገረመኝ ነው:: ለወትሮው *ጡ ላይ መርፌ እንደተሰካበት ሰው አሁን አሁን በእረፍት (break) ስም ስወጣና ሰገባ ነበር ሰዓቱ ያልቅ የነበረው:: ለሶስት ሰዓት ስቀመጥ ታዲያ ያነበብኩት ሳይኮሎጂ ነው:: ሳብጀክቱን አወደዋለሁ:: እሺ ብለው ከሚነበቡልኝ ትምህርቶች አንዱ ነው:: ሌላ እሺ ብሎ የሚነበብልኝ....ሌላ....ሌላ....የለም:: ሃይ ስኩል ከልቤ እመሰጥበት የነበረው ባዮሎጂ እንኩዋን እጅ እጅ ብሎኛል::በእርግጥ ሂሳብና ፊዚክስ ካልኩሌሽኖች መስራት አሁንም ድረስ አልሰለቸኝም:: ግን በቃ ገና ሚድ ሴሚስተር ፈተናችንን እንኩዋን ሳንወስድ ምነው ይህ አንደኛ ዓመት ወደዚያ አልቆ በተገላገልኩት እላለሁ.... ወደ እውነተኛው ሜዲስን ትምህርት እስከምንሸጋገር ቸኩያለሁ:: ከአንደኛው ሴሚስተር በሁዋላ ፍረሽማን እንጨት እንጨት ብሎኛል:: በነገራችን ላይ ሚድ ሴሚስተር ፈተና ልንወስድ የቀረን አንድ ሳምንት ቢሆን ነው::

ይልቅስ ዛሬ አንድ ደስ የሚል ደብዳቤ ከቤተሰብ ደረሰኝ:: ላኪው አባቴ ነው::ለ አንድ መቶ ስድስት ቀናት ታስሮ ከነበረበት ሆለታ ገነት የሚገኝ አስር ቤት መፈታቱን የሚገልፅ የብስራት ደብዳቤ ነው:: ቅኑና መምህሩ አባቴ ያለፈው መንግስት ባቋቋመው የሰራተኞች ፓርቲ ውስጥ ተሳትፎ ነበረህ በሚል በተመሳሳይና ተመሳሳይ ባልሆነ ምክንያት ከታሰሩ ከሌሎች እልፍ ጎልማሶች ጋ ያሳለፈውን የእስር ግዜ ጨረሰ:: በእውነቱ እኔ በጣም ደስ ያለኝ ከሁሉም በላይ ለእናቴ ነው:: ብቸኛ የገቢ ምንጭ የነበረ ባል በሌለበት በድንገት  የብዙ የቤተሰብ ኃላፊና አስተዳዳሪ መሆን ይከብዳል:: አባቴ ታስሮ ይህን ቀን ሳድግ አይስጠኝ የሚያስብሉ በርካታ በሀዘን የተሞሉ ረዥምና ደባሪ የችግር ቀናት ከእናቴ፣ ከወንሜና ከእህቶቼ ጋ አሳልፌ ነበር:: ክረምቱን ሙሉ ከቤት የተለየው አባቴ እስር ቤት እያለ ነው እኔ ወደዚህ የመጣሁት:: በአንድ በኩል በጮርቃው አስተሳሰቤ ወደዚህ መምጣቴን ወድጀዋለሁ። ይብላኝ ለወንድምና እህቶቼ እንጂ የቤቱን የለት ተለት ችግርና አበሳ ከመጋፈጥ ተገላግያለሁ:: ነገር ግን በየቀኑ በአይን የማይታይ አንዳች መግነጢሳዊ ገመድ ልቤን ወደቤቴ ክፉኛ ይስበው ነበር:: ይህ ቁልጭ ብሎ የታወቀኝ ዛሬ የአባቴን መፈታት ስሰማና ከላዬ ላይ አንዳች ነገር ዱብ ብሎ የወረደ ያህል የመንፈስ ቅለት ሲሰማኝ ነው.......እነሆ ለሌሎችም ሁሉ ቸር ያሰማልኝ

Thursday, October 23, 2014

ካለፈው የለጠቀ

ካለፈው የለጠቀ......


መምህራኖቻችንን እየጠላሁዋቸው በመሄድ ላይ እገኛለሁ:: ባለፈው የገለፅሁት አጠቃላይ የጤና ሳይንሱ ሁኔታ ያሳደረብኝ የተስፋ መገመስ: እሱንም ተከትሎ የመጣው ትምህርት መጥላቴ ሳያንስ የአስተማሪዎቻችን ለኛ ያለማሰብ በብርቱ እንድጠላቸው አደረገኝ:: ከልባቸው እኛን እውቀት ለመመገብ ሳይሆን የተሰጣቸውን ካሪኩለም በቀነ ገደቡ ለመጨረስ ይመስላል ከተወሰነው የሌክቸር ሰዓት በላይ ያለማቁዋረጥ ይናገራሉ:: በነገራችን ላይ ከደርግ መውደቅ ቀደም ብሎ በአንደኛው ሴሚስተር ሲያስተምሩን ከነበሩት ውስጥ አብዛኞቹ ኤርትራውያን የነበሩ ሲሆን ግልፅ በሆነ ምክንያት ባሁኑ ግዜ የሉም:: እነሱ በልምድም ሆነ በእድሜ የጎለበቱ የነበሩ ሲሆን በዚህ ሴሚስተር የማያቸው ግን አንድ ፍሬ ና ልምድ የሌላቸው ናቸው:: አንዳንዶቹ በመሰረቱ ሌክቸር ሲሰጡ ድምፃቸው የማይወጣና የማይወርድ ምንም አይነት ዜማ ወይም ቅላፄ የሌለው ለዛ ቢስ ከመሆኑ የተነሳ ማሰልቸት ብቻ ሳይሆን እነሱን ተቀምጦ ማዳመጥ ያማል:: በዋናው ሰዓት ከተፈቀደው ገደብ አልፈው እያስተማሩ እንኩዋን ለማለት ያሰቡትን ብለው ስለማይጨርሱ ሜክ አፕ ክላስ ብለው ከሰዓት በሁዋላ እየጠሩ በንግግር ያጥለቀልቁናል:: በነሱ ቤት ማስተማራቸው ነው:: ድንቄም

ሌላው በጣም እየከነከነኝ ያለ ነገር ደግሞ ወደፊት ልንጀምረው ከስድስት ወር ያነሰ ግዜ ከቀረን የህክምና ሙያ ትምህርት ጋር ምንም አይነት ተዛማጅነት የሌላቸው ትምህርቶች እየተማርን መሆኑ ነው:: በተለይ አንድ ሶሺዮሎጂ የሚባል ትምህርት አለ:: ከትምህርቱ ማስጠላት የሚያስተምረን ብስል ቀይ ባለ ግዙፍ አፍንጫ ጮርቃ መምህር ሞዛዛነት! በቃ ጨጉዋራዬን ነው የሚልጠኝ:: ከብዙ ሌሎች ሰብአውያን ፊት ቁሞ ሌክቸር ለመናገር ይቅርና የግል ሃሳቡን ለሌላ ሰው ማካፈል መቻሉን እጠራጠራለሁ:: እንዴት ለመምህርነት ታጨ? ጥያቄው ለራሴ ና ለውስጤ ነው:: ባዮሎጂ መምህራችንም ቢሆን ከሶሺሎጂው ጥቂት ብቻ ነው የሚለየው:: ንግግሩ የማይጨበጥ ና በእንከን የተሞላ ነው:: እንግዲህ ከእንደዚህ አይነት አድካሚ ተናጋሪዎችና ንግግሮቻቸው በሁዋላ ወደ ቀዮ የሸክላ አዳራሽ ስሄድ ለሌላ አስከፊ ጅጤሳ ገፅታ እጋለጣለሁ..በዚህ ግዙፍ አዳራሽ ውስጥ ከአልጋዎችና ፊትለፊቶቻቸው እንደ ጅብራ ከተጋረጡት ቁም-ቁጭ ሳጥኖች በስተቀር ቁጭ ብሎ ለማንበበቢያ የሚሆን ወንበርና ጠረጴዛ የለም.....ላይብረሪ መሄድ ግድ ይላል....