Thursday, November 13, 2014

ሚድ ሴሚስተርና የአብይ ማስታወሻ


ጥቅምት ሃያ ሁለት አስራዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት አ.ም.

ሚድ ሴሚስተርና የአብይ ማስታወሻ
ከጥቅምት 18 እስከ 22 ባሉት ቀናት ውስጥ የ ግማሽ ሴሚስተር ፈተናዎቻችንን ወሰድን:: በእንግሊዝኛ ተጀምሮ : በኦርጋኒክ ኬሚስትሪ: ሳይኮሎጂ: ሶሺዮሎጂ :ፊዚክስ ና ማትስ ተከትሎ በ ባዮሎጂ ተጠናቀቀ:: እንግሊዝኛና ኦርጋኒክ ኬሚስትሪ ሁለቱም ከብደውኝ የነበረ ሲሆን: ሳይኮሎጂ ደግሞ ስለምወደውና በደንብ ስላነበብኩም ነው መሰል ቀሎኝ ነበር:: ፊዚክስ የጠበኩትን ያህል አልከበደኝም:: ሶሺዮሎጂ ግን የማልወደው ትምህርት ከመሆኑም ሌላ ፈተናውንም በሚገባ እንደማልወጣው አስቀድሜ ስለደመደምኩ ግዜ ሳላባክን በፍጥነት ነው ከፈተናው ከፍል የወጣሁት:: ጉዋደኞቼ ሳይገርማቸው አይቀርም::  በነገራችን ላይ በሚድ ሴሚስተር ፈተና ቀናት መሃል አንድ ምሽት የአንደኛ ሴሚስተር ውጤት ወረቀቴን ባጋጣሚ መፃሕፍ ቅዱሴን ስገልጥ አየሁት:: በጣም ማስደሰት ብቻ ሳይሆን ልክ የሌላ ሰው የሆነ ያህል አስቀናኝ:: እንደገና ደግሜ እንደማላመጣው ተሰምቶኝ ይሆናል:: 3.84 ይላል አጠቃላይ ነጥቡ.....ባጠቃላይ ስለ ሚድ ሴሚስተር ፈተና ጥሩ ስሜት አልተሰማኝም:: በደንብ አልሰራሁም:: ቢሆንም ባይሆን ብዬ ለዋናው የሴሚስተር ፈተና በርትቼ ለማጥናት በሚስጥር ለራሴ ቃል ገባሁ:: 

ባዮሎጂ ፈተናችንን የወሰድን እለት ከ ቀርብ ጉዋደኞቼ አንዱ የሆነው አብይ በጠየኩት መሰረት አጀንዳዬ ላይ የሚከተለውን ፅሁፍ አሰፈረ..


መጀመሪያ ብዕሬን በግል ማስታወሻህ ላይ እንድፈትን ዕድል ስለተሰጠኝ በጣም እግዜር ይስጥልኝ:: ስዎች ከራሳቸው አፍልቀው በሚፅፉት ከገፆች አልፈው ወደ መፅሐፍት ሲሸጋገሩ መስማት እጅግ በጣም ያስደንቀኛል::  በእውነቱ
እኔ እቺን ገፅ እንኩዋን ለመሙላት በጣም ነው የማንገራግረው::

ራሴን ሳላስተዋውቅ: ብዙ ያወራሁ መሰለኝ:: አብይ ሕሩይ እባላለሁ:: ትውልዴ አዲስ አበባ ከፍተኛ 11 ቀበሌ 02 በተለምዶ ስሙ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ነው:: ጅማን መዋያ ማደሪያዬ ያደረኩት የካቲት 12 ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤትን ወክለው ወደ ጅጤሳ ከመጡት “the magnificent three” ጋር ከመስከረም ፩፮ ፩፱፰፫ ጀምሮ ነው::

ስለራሴ ይህን ካስተዋወኩዋችሁ ዘንዳ አሁን ሰዓቱ ከምሽቱ ፮ መሆኑን ልንግራችሁ እወዳለሁ:: ዛሬ ፍፁም ነፃነት ተሰምቶኝ ነው የዋልኩት:: የ mid-semester ፈተናዎች ማሳረጊያ የሆነው ባዮሎጂን ጨርሰን በምሽቱ የቪዲዮ ትርኢት Police Academy የተባለውን አዝናኝ ፊልም ስመለከት ነው ያመሸሁት:: በእውነቱ ከሆነ ከፊልም አፍቃሪዎች መሃከል አንዱ ነኝ:: አላዘውትር እንጂ ፈተና በደረሰበት ሰሞን እንኩዋን ገብቼ ማየት የፊልም ፍላጎቴን ያረካልኛል:: የዛሬውን ምሽት show ለየት ያደረገው በቪዲዮ ማሳያው አዳራሽ በኩል ሲያልፉ እንኩዋን የሚሰቀጥጣቸው ሴቶች እህቶቻችን ሁለት ወንበር ለመጋራት መብቃታቸው ነው::


ነገ እሁድ ነው:: ጥሩ መደበሪያ ቦታ እንደሚያስፈልገኝ በማውጠንጠን ላይ ነኝ:: እንዲያውም አንድ በጣም የልብ ጉዋደኛዬ የሆነ ከአዲስ አበባ የመጣ ወዳጄን ጅጤሳን የማስጎብኘት ሃሳቡ መጥቶልኛል:: በዚሁ እሰናበታለሁ::

No comments:

Post a Comment