አሁንም የቀጠለ
ይህ እንግዲህ የህክምና ትምህርት ቤት ወግ ስለሆነ አንዳንድ አንባብያንን እንዳያሰለች ስጋት አለኝ:: ነገር ግን ምንም ማድረግ አልችልም::
ጥቅምት አስራ አንድ አስራ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አራት አ.ም.
ባለፈው ተሳክቶልኝ ላይብረሪ ውስጥ ለሶስት ሰዓት ያለማቁዋረጥ ተቀመጥኩ:: እስከአሁን ድረስ እየገረመኝ ነው:: ለወትሮው *ጡ ላይ መርፌ እንደተሰካበት ሰው አሁን አሁን በእረፍት (break) ስም ስወጣና ሰገባ ነበር ሰዓቱ ያልቅ የነበረው:: ለሶስት ሰዓት ስቀመጥ ታዲያ ያነበብኩት ሳይኮሎጂ ነው:: ሳብጀክቱን አወደዋለሁ:: እሺ ብለው ከሚነበቡልኝ ትምህርቶች አንዱ ነው:: ሌላ እሺ ብሎ የሚነበብልኝ....ሌላ....ሌላ....የለም:: ሃይ ስኩል ከልቤ እመሰጥበት የነበረው ባዮሎጂ እንኩዋን እጅ እጅ ብሎኛል::በእርግጥ ሂሳብና ፊዚክስ ካልኩሌሽኖች መስራት አሁንም ድረስ አልሰለቸኝም:: ግን በቃ ገና ሚድ ሴሚስተር ፈተናችንን እንኩዋን ሳንወስድ ምነው ይህ አንደኛ ዓመት ወደዚያ አልቆ በተገላገልኩት እላለሁ.... ወደ እውነተኛው ሜዲስን ትምህርት እስከምንሸጋገር ቸኩያለሁ:: ከአንደኛው ሴሚስተር በሁዋላ ፍረሽማን እንጨት እንጨት ብሎኛል:: በነገራችን ላይ ሚድ ሴሚስተር ፈተና ልንወስድ የቀረን አንድ ሳምንት ቢሆን ነው::
ይልቅስ ዛሬ አንድ ደስ የሚል ደብዳቤ ከቤተሰብ ደረሰኝ:: ላኪው አባቴ ነው::ለ አንድ መቶ ስድስት ቀናት ታስሮ ከነበረበት ሆለታ ገነት የሚገኝ አስር ቤት መፈታቱን የሚገልፅ የብስራት ደብዳቤ ነው:: ቅኑና መምህሩ አባቴ ያለፈው መንግስት ባቋቋመው የሰራተኞች ፓርቲ ውስጥ ተሳትፎ ነበረህ በሚል በተመሳሳይና ተመሳሳይ ባልሆነ ምክንያት ከታሰሩ ከሌሎች እልፍ ጎልማሶች ጋ ያሳለፈውን የእስር ግዜ ጨረሰ:: በእውነቱ እኔ በጣም ደስ ያለኝ ከሁሉም በላይ ለእናቴ ነው:: ብቸኛ የገቢ ምንጭ የነበረ ባል በሌለበት በድንገት የብዙ የቤተሰብ ኃላፊና አስተዳዳሪ መሆን ይከብዳል:: አባቴ ታስሮ ይህን ቀን ሳድግ አይስጠኝ የሚያስብሉ በርካታ በሀዘን የተሞሉ ረዥምና ደባሪ የችግር ቀናት ከእናቴ፣ ከወንሜና ከእህቶቼ ጋ አሳልፌ ነበር:: ክረምቱን ሙሉ ከቤት የተለየው አባቴ እስር ቤት እያለ ነው እኔ ወደዚህ የመጣሁት:: በአንድ በኩል በጮርቃው አስተሳሰቤ ወደዚህ መምጣቴን ወድጀዋለሁ። ይብላኝ ለወንድምና እህቶቼ እንጂ የቤቱን የለት ተለት ችግርና አበሳ ከመጋፈጥ ተገላግያለሁ:: ነገር ግን በየቀኑ በአይን የማይታይ አንዳች መግነጢሳዊ ገመድ ልቤን ወደቤቴ ክፉኛ ይስበው ነበር:: ይህ ቁልጭ ብሎ የታወቀኝ ዛሬ የአባቴን መፈታት ስሰማና ከላዬ ላይ አንዳች ነገር ዱብ ብሎ የወረደ ያህል የመንፈስ ቅለት ሲሰማኝ ነው.......እነሆ ለሌሎችም ሁሉ ቸር ያሰማልኝ