Sunday, October 19, 2014

መስከረም ፪፪ ቀን ፩፱፰፬ አ.ም. ሐሙስ 

ዳግም ሲጀመር

እነሆ መስቀል አለፈ:: መቸም መስከረም ደስ የሚል ነገር አለው:: የአዲስ ዓመት መግቢያ: የአደይ አበባ ማበቢያ ና መፍኪያ ወር..... ለክርስትያኖች መስከረም አንድ ቀን በቅዱስ ዮሐንስ የተጀመረው ያመት በዓል ግርግር መስቀል ካለፈ በሁዋላ ጋብ ይላል:: ለብዙዎች መስከረም የተሃድሶና የተስፋ ወር ነው:: ለኛ ለ ጅጤሳ ተማሪዎች ግን የወደፊት ተስፋችንን ሰንቀን ትምህርታችንን በቅጡ እንዳንማር የሚያደርጉ ሁኔታዎችን በየጊዜው የምናይበት ሆነ የዘንድሮው መስከረም:: ባለፈው እንዳልኩት በጤና ሳይንሱ ውስጥ  ትምህርት ተብሎ አሁን እየተካሄደ ያለው ነገር የውሸት የውሸት መስሎ ነው የሚሰማኝ:: እንዲሁ ትምህርት እየተካሄደ እንዳለ ለማሳየት የሚደረግ ጥረት ይመስለኛል:: ለማን እንደሆን ማሳየት የተፈለገው አልገባኝም:: ለኛ ይሆን? በየቀኑ የማያቸውና የምሰማቸው ግዙፍ የሂደት ክፍተቶች አሉ:: በዚህ ሁኔታ ትምህርቴን መከታተልና ማጥናት አልቻልኩም:: ተስፋ ሊኖር ይገባል ለካ ለመንቀሳቀስ: ለመስራት: ለመቀጠል ወዘተ .......አንዳንዴ በአንክሮ አስብ: አስብና ኢትዮጵያ ውስጥ ራሱ መማር ትርጉም አጥቶብኝ ተስፋ እቆርጣለሁ::

የጤና ሳይንሱ ዲፕሎማ ተማሪዎች በሙሉ አመፅ ላይ ናቸው:: ትምህርት በራሳቸው ጊዜ ካቆሙ ሰነበቱ:: በብላቴው ዘመቻ ምክንያት ትምህርት ለስድስት ወር ቢቁዋረጥም በስልጠናቸው ላይ ሌላ ስድስት ወር እንዲጨመር ሲል ጤና ሳይንሱ ያሳለፈውን ውሳኔ አልፈለጉትም:: እነሱ የሚፈልጉት በምንም ይሁን በምን የሚመረቁበት ጊዜ ከብላቴ ዘመቻ በፊት በታሰበው እንዲሆን ነው::

ባለፈው የህክምና ተማሪዎችን ያስተምሩ የነበሩ ኩባውያን በሙሉ የመንግስቱን ለውጥ ተከትሎ ወደ ሀገራቸው በመመለሳቸው ከፍተኛ የሆነ የሁለተኛና የሶስተኛ ዓመት Basic Science መምህራን እጥረት አለ:: ከግብፅና ከህንድ መምህራን ለማስመጣት ጥረት እየተደረገ እንዳለ ይሰማል: ግን ይህንን በቀላሉ ላምን አልቻልኩም: አዝናለሁ  ነባራዊ ሁኔታዎች ያስከተሉብኝ ተጠራጣሪነት ነው እንዲህ ያረገኝ:: የሁለተኛ ዓመት የህክምና ተማሪዎች ከነገ ጀምሮ ከፍል እንደማይገቡ ሰምቻለሁ:: ግቢው ውስጥ ያሉ አንዳንድ አበሻ ረዳት መምህራን እያስተማሩዋቸው ነበር:: ተማሪዎቹ ግን በዚያ መቀጠል አልፈለጉም:: 

ሌሎችም የተለያዩ ችግሮች አሉ.....እውን ጅጤሳ ከመንግስት ትኩረት ተሰጥቶት እየተንቀሳቀሰ ነው? የሚል ጥያቄ ባእምሮዬ ይመላለሳል:: አንዳንዴ በድንገት ጥቁር አንበሳ በሚማሩ የህክምና ተማሪዎች እቀናለሁ:: ደሞኮ እንደሰማሁት ከሆነ አዲስ አበባ ያሉ እንደነ ፕሮፌሰር አስራት ያሉ ሀኪሞች ጅጤሳን በእኩል ደረጃ አያዩትም:: መጀመሪያም ሲቁዋቁዋም ደስ አላላቸውም ነበር ይባላል:: ለኔ የሚሰማኝ ጅጤሳ በግድ ባንድ ሰው (በመንግስቱ) ፍላጎት የተመሰረተ የተማሪዎች ሞራል መግደያና ማሰቃያ ሆኖ ነው:: በዚያ ላይ ከተማው ዉሃ ያጥረዋል:: የሙቀቱስ ነገር!

ከስድስት ወራት በፊት ከዚህ ለተመረቁት ዶክተሮች ደስታ ሳይሆን ሃዘን ተሰማኝ በስቃይ ውስጥ እንዳለፉ በመገመት:: ለኔ ገና ለምጀምረው ደግሞ ፈራሁለት.....

No comments:

Post a Comment