Thursday, October 23, 2014

ካለፈው የለጠቀ

ካለፈው የለጠቀ......


መምህራኖቻችንን እየጠላሁዋቸው በመሄድ ላይ እገኛለሁ:: ባለፈው የገለፅሁት አጠቃላይ የጤና ሳይንሱ ሁኔታ ያሳደረብኝ የተስፋ መገመስ: እሱንም ተከትሎ የመጣው ትምህርት መጥላቴ ሳያንስ የአስተማሪዎቻችን ለኛ ያለማሰብ በብርቱ እንድጠላቸው አደረገኝ:: ከልባቸው እኛን እውቀት ለመመገብ ሳይሆን የተሰጣቸውን ካሪኩለም በቀነ ገደቡ ለመጨረስ ይመስላል ከተወሰነው የሌክቸር ሰዓት በላይ ያለማቁዋረጥ ይናገራሉ:: በነገራችን ላይ ከደርግ መውደቅ ቀደም ብሎ በአንደኛው ሴሚስተር ሲያስተምሩን ከነበሩት ውስጥ አብዛኞቹ ኤርትራውያን የነበሩ ሲሆን ግልፅ በሆነ ምክንያት ባሁኑ ግዜ የሉም:: እነሱ በልምድም ሆነ በእድሜ የጎለበቱ የነበሩ ሲሆን በዚህ ሴሚስተር የማያቸው ግን አንድ ፍሬ ና ልምድ የሌላቸው ናቸው:: አንዳንዶቹ በመሰረቱ ሌክቸር ሲሰጡ ድምፃቸው የማይወጣና የማይወርድ ምንም አይነት ዜማ ወይም ቅላፄ የሌለው ለዛ ቢስ ከመሆኑ የተነሳ ማሰልቸት ብቻ ሳይሆን እነሱን ተቀምጦ ማዳመጥ ያማል:: በዋናው ሰዓት ከተፈቀደው ገደብ አልፈው እያስተማሩ እንኩዋን ለማለት ያሰቡትን ብለው ስለማይጨርሱ ሜክ አፕ ክላስ ብለው ከሰዓት በሁዋላ እየጠሩ በንግግር ያጥለቀልቁናል:: በነሱ ቤት ማስተማራቸው ነው:: ድንቄም

ሌላው በጣም እየከነከነኝ ያለ ነገር ደግሞ ወደፊት ልንጀምረው ከስድስት ወር ያነሰ ግዜ ከቀረን የህክምና ሙያ ትምህርት ጋር ምንም አይነት ተዛማጅነት የሌላቸው ትምህርቶች እየተማርን መሆኑ ነው:: በተለይ አንድ ሶሺዮሎጂ የሚባል ትምህርት አለ:: ከትምህርቱ ማስጠላት የሚያስተምረን ብስል ቀይ ባለ ግዙፍ አፍንጫ ጮርቃ መምህር ሞዛዛነት! በቃ ጨጉዋራዬን ነው የሚልጠኝ:: ከብዙ ሌሎች ሰብአውያን ፊት ቁሞ ሌክቸር ለመናገር ይቅርና የግል ሃሳቡን ለሌላ ሰው ማካፈል መቻሉን እጠራጠራለሁ:: እንዴት ለመምህርነት ታጨ? ጥያቄው ለራሴ ና ለውስጤ ነው:: ባዮሎጂ መምህራችንም ቢሆን ከሶሺሎጂው ጥቂት ብቻ ነው የሚለየው:: ንግግሩ የማይጨበጥ ና በእንከን የተሞላ ነው:: እንግዲህ ከእንደዚህ አይነት አድካሚ ተናጋሪዎችና ንግግሮቻቸው በሁዋላ ወደ ቀዮ የሸክላ አዳራሽ ስሄድ ለሌላ አስከፊ ጅጤሳ ገፅታ እጋለጣለሁ..በዚህ ግዙፍ አዳራሽ ውስጥ ከአልጋዎችና ፊትለፊቶቻቸው እንደ ጅብራ ከተጋረጡት ቁም-ቁጭ ሳጥኖች በስተቀር ቁጭ ብሎ ለማንበበቢያ የሚሆን ወንበርና ጠረጴዛ የለም.....ላይብረሪ መሄድ ግድ ይላል....

No comments:

Post a Comment