Tuesday, September 15, 2015

ሰኞ ጥቅምት 16 ቀን 1985 አ.ም.  ከምሽቱ 7 ሰዓት ከ 11 ደቂቃ
የኔ ውድ በየቀኑ ከሚከሰቱትና ከሚያጋጥሙኝ በርካታ ክስተቶች አብዛኞቹን ከቁጥር ባላስገባቸውና ባላስተውላቸውም የተወሰኑት ግን ለማመን እስከሚያዳግተኝ ድረስ የሚገርሙኝ ናቸው:: እንደዚህ አይነቶቹ ክስተቶች ያጋጣሚ ብቻ እንዳልሆኑ ለልቤ ዘወትር ይሰማዋል::  ዛሬ ታዲያ እንዲህ ልል የቻልኩት ለምን ይመስልሻል? ነገሩ እንዲህ ነው....በሕቡዕ-ጠማማው መምህር  ምክንያት የማይመቸኝና የሚጎረብጠኝ የፊዚዮሎጂ ትምህርት ግማሽ ሴሚስተር ፈተና ነገ ስለሆነ ሰሞኑን እንደመስሎቼ ሁሉ ሌላውን ትምህርት ወደ ጎን በመተው እሱ ላይ ብቻ ለማተኮርና ዘለግ ያለ ንባብ ለማድረግ ሞክሬ በቅጡ አልተሳካልኝም ነበር:: እናም ስለፈተናው ባደረብኝ ስጋት የተነሳ ምነው በቀረ እያልኩ በሆዴ ከመቶ ግዜ በላይ አሰላሰልኩ:: ታዲያ ምን ቢሆን ጥሩ ነው? ዛሬ ጠዋት ራሱ ሕቡዕ-ጠማማው መምህር ፈተናው መቅረቱን ለሁላችንም ነገረን:: አንዳች ከትከሻዬ ላይ ዱብ ሲል በእርግጥ ተሰምቶኛል:: ፈተናው በአንድ ሳምንት ተላለፈ:: እግዚአብሔር ይመስገን.....


ሰኞ ጥቅምት 23 ቀን 1985 አ.ም. 
ነገ ደግሞ እኔ የምወደውና ከልቤ የምመሰጥበት የአናቶሚ ትምህርት የቃል (oral exam) ፈተና ይጀመራል በመባሉ እገሌ ከገሌ ሳይል መላ ፒሲዋን የአናቶሚ ደብተሩና ማስታወሻው እንዲሁም ስዕሉ ላይ አድፍጧል:: የዶርሜ አባላት በሙሉ የሉም:: እንደታዘብኩት ከሆነ ሌክቸር ላይ መገኘት ካቆሙ የሰነበቱም አሉ::  ይህ እንግዲህ ለግማሽ ሴሚስተር ፈተና ማለት ነው:: ታህሳስ ውስጥ ዋናው ፈተና ሲመጣ ምን ማድረግ ያቆሙ ይሆን? ወደኔ ስመጣ ትናንት Thorax የተሰኘውን ቻፕተር በሙሉ ለማንበብ አቅጄ እንደተለመደው እቅዱን ከግብ ሳላደርስ ወደ መኝታዬ ያመራሁ ሲሆን ዛሬ ደግሞ ከቀኑ አስር ሰዓት ጀምሮ በንባብ የወገምኩትን Abdomen የስተሰኘውን ክፍል እንደትናንትናው ሁሉ ሳልጨርስ ልተኛ ተቃርቢያለሁ:: ይህም እንግዲህ ለግማሽ ሴሚስተር ፈተና መሆኑን ልብ በይ:: ነገ እኔም እንደ አንዳንድ ከላይ እንደተጠቀስኩዋቸው ወገኖቼ ሁሉ ምንም አይነት ሌክቸር ላይ ላለመገኘት ለውስጤ ቃል ገብቼለታለሁ:: እንደሌሎቹ በድጋሚ የማንበብ ዕድል ባይኖረኝ እንኩዋ አንድ ዙሩን ራሱ ጨርሼ ለማንበብ እሞክራለሁ:: የአናቶሚን ፈተና ሁኔታ ከሌላው ጊዜ የበለጠ ከባድ የሚያደርገው ደግሞ ፈተናው የቃል ፈተና መሆኑና ነገ የተወሰንነው ብቻ የምንፈተን መሆኑ ነው:: ነገ ያልደረሰው ለከነገወዲያ ማለት ነው:: ከነገወዲያ ያልደረሰው ለቀጣዩ ቀን... እያለ ይቀጥላል:: ነገ ማ እንደሚፈተን ማ እንደማይፈተን ማንኛችንም አናውቅም:: ስለዚህም ሁሉም የአጠናንን ፍጥነቱን የመተረው “ነገ እፈተናለሁ!” በሚል እሳቤ ነው::

ማክሰኞ ህዳር 1 ቀን 1985 አ.ም.

በጅማ ህወቴ ውስጥ እንደዛሬ ንዴቴ ጫፍ ላይ ደርሶ ምንም ነገር ለማድረግ እስካለመቻል ደርሼ አላውቅም:: ምክንያቱ እንዲህ ነው:: ባለፈው ማክሰኞ ይጀመራል ተብሎ የነበረው የአናቶሚ የቃል ፈተና በተባለው ቀን ሳይጀመር ቀርቶና በሶስት ቀን ዝግይቶ በቀን ለአምስትና ስድስት ልጆች ብቻ የሚደርስ ከመሆኑም ባሻገር አመራረጡ በዘፈቀደ ስለነበር እኔና ሌሎች ዘጠኝ ልጆች  ሳይቀናን ቀርቶ ስንገዋለል ወደ ዛሬ ደረስን:: ያናደደኝ ግን ይህ አይደለም:: ፕሮፌሰር ስላህ ከአስራችን ውስጥ አምስቱን ከፈተነ በሁዋላ የቀረነውን አምስት ልጆች ዛሬም ሳይፈትነን ቀረ:: እንደነገሩ ጥሎን ሄደ:: ካሁን ካሁን ስሜ ይጠራል እያልኩ ጆሮየንና አይኔን ማቁልጭልጬ አልጠቀመኝም:: ሳምንቱን ሙሉ አናቶሚ ላይ ብቻ ተኝቼ መክረሜ አበሳጨኝ:: በገንኩኝ:: አረርኩኝ::  የአምስታችን የቀረነው ልጆች ተራ ከሁለት ቀን በሁዋላ ሐሙስ እንደሆነ ተነግሮናል:: እስከዚያ ስንቱን እረሳው ይሆን? የፈለገው ይሁን እንጂ ካሁን በሁዋላ ለአናቶሚ ቅንጣት ታክል ደቂቃ አላባክንም! የሚገርመውና የሚያስፈራው ሀቅ ሌሎቹ የተፈተኑት ባገኙት እፎይታ በመንተራስ ልሎች ትምህርቶችን በእርጋታ ማጥናት መቀጠላቸው ነው! ይህ በእውነቱ አድልዎ ነው:: ምን በደልን? ምን አደረግን?

............የኔ ውድ ብታምኚም ባታምኚም በዚህ ብስጭት ውስጥ ሆኜ በዶርም ቁጥር 207 መስኮት አሻግሬ ሙሉ ጨረቃን በሰማያዊው ሰማይ ላይ ተንሳፋበት አየሁዋት:: በዚህም የተነሳ በድገት ፍቅር ፍቅር አለኝ:: በምልሰት የበለጠ ልጅ እግር ወደነበርኩበት ወደ ህዳር 1982 አ.ም. ሄጄ አንድን ነገር አስታወስኩ ....የወጣት ትዝታ...መልካም ትዝታ................

No comments:

Post a Comment