Wednesday, February 8, 2017

ከመስከረም 4 እስከ መስከረም 9 1988 አ.ም.

አርብ መስከረም 4 ቀን ጠዋት ተኝተው ከሚታከሙ ህመምተኞቼ አንዱ በውጋት እየተሰቃየ ሲጮህ ደረስኩ:: ወደሆስፒታል መኝታ ከፍል እንዲገባ የተደረገበት ምክንያት በብልቱ ውስጥ የሚያልፈው የሽንት ቱቦ በቆየ ጠባሳ ምክንያት ተዘግቶ አላሸና ብሎት ነው (Urethral Stricture):: የዚያን ለት ጠዋት ፊኛው ሞልቶና መሽኛው ሙሉ በሙሉ ተዘግቶ ስለነበር ውሃ ሽንቱ በየት ይውጣ?! በከፍታኛ ሁኔታ አመመው:: እጆቹን ፊኛው  ላይ ለጥፎና ተጣጥፎ እየተንፈራፈረ ይጮሃል:: በረዥሙና ሞላላው ስርጅካል መኝታ ክፍል ውስጥ  የነበሩ ሌሎች ህሙማን በሱ ሁኔታ ሁከት ውስጥ ገቡ: ተሸበሩ::  ህመመተኛ በአስቸኩዋይ ወደ ቀዶ ጥገና ክፍል እንዲወሰድ በመወሰኑ የዚያ ቀን ያልጋ ዙሪያ ትምህርት (Bed Side) ተሰረዘ:: እኔም ቀዶ ጥገና ክፍል ውስጥ ከቀዳጅ ሐኪሙ ጋር በመግባት የህመመተኛ ሆድ ተቀዶ የሽንት ፊኛው ውስጥ (Urinary Bladder) ሰው ሰራሽ ቱቦ (Catheter) ሲገባለት አየሁ:: ረዳት (Assistant) በመሆን አገለገልኩ:: በዚህም አነስ ያለች ኩራት ተሰማችኝ:: ህመምተኛው ከቀዶ ጥገናው በሁዋላ እፎፎፎፎይ አለ:: ለጊዜው ሽንቱ ሁሉ በበሰው ሰራሽ ቱቦው በኩል ስለሚወጣ ሽንቴ መጣብኝ: የት ልሽና ገለ መለ ብሎ መነቅ አያስፈልገውም:: ነገር ግን የችግሩ ሁሉ ምንጭ የሆነው ጠባሳ ገና ስላልተቀረፈ ሌላ ቀዶ ጥገና ይጠብቀዋል::

ቅዳሜ መስከረም 5 ቤተ መጽሐፍት ውስጥ ነበርኩ:: ላለሁበት ቡድን የማርበው ዲስኩር (presentation) ስለነበር በትጋት ማንበብ ነበረብኝ:: የኝን አርስት አልወደድኩትም:: “Lung Nodules” ይላል:: ያልተለመደ አርስት ነው:: የሚነበብ ሰብሰብ ያለ መረጃ ስላገኘሁ ጭንቀት የወለደው ብስጭት በጣም ተበሳጨሁ:: ምንም አማራጭ ስላልነበረኝ ማንበቤን ቀጠልኩ : ይባስ ብዬ እሁድንም በተመሳሳይ ተግባር አሳለፍኩ:: የቀርበው ማክሰኞ ስለሆነና ሰኞ ደሞ በሌሎች ትምህርታዊ ሂደቶች ስለምጠመድ የዲስኩሩን ዘገባ እሁድ ማጠናቀቅ የግድ ነበር:: 

ሰኞ መስከረም 7 አዲስ ጉዋደኛ አገኘሁ:: አንድ ወጣት የጅጤሳ መግቢያ በር ላይ ይጠብቅሃል ተብዬ ስሮጥ ሄድኩ:: በኔው የእድሜ ክልል ያል ፊቱ ጠቆር የሚል መልኩ ግን የሚያምር የሚመስል አፍንጫ ሰልካካ  ፀጉረ ሉጫ ፈገግተኛ ሰው:: ያደኩበት ሰፈር ልጅ እንደሆነ ወዲያውኑ አወቅሁ:: ከዘህ በፊት እንዳየሁት እርግጠኛ ነኝ:: ግን በትክክል እንዴት እንደማውቀው ተረሳኝ:: ሰላምታ ተለዋውጠን ስማችንን ተዋውቅን:: ግን የኔን ነገርኩት እንጂ የሱን በቅጡ አልሰማሁትም ነበር:: ለአምስት ወራት የስራ  ቆይታ ወደጅማ እንደመጣ ነገረኝ:: በቅርቡ አዲስ አበባ ከሚገኘው ከተማ ፕላን ኮሌጅ (Town Planning College) በምህንድስና እንደተመረቀ ነገረኝ:: በጅማ የሚገኘውን የመድህን ድርጅት ህንፃ እድሳት ለመከታተል ነው የመጣው:: አንደኛ ደረጃ የሄድነው አንድ ትምህርትቤት ነው::  ትንሽ ካወራን በሁዋላ ለሚቀጥለው ን ተቀጣጥረን ተለያየን::  በማግስቱ ከቀኑ አስር ሰዓት መጣ :: ስሙን አሁን አውት ጌታሁን ይባላል:: ጥሩ አቀራረብ ያለው ልጅ ነው:: ተመቸኝ::  እንደገና ለነገ ከሰዓት ተቀጣጥረን ተለያየን::


ማክሰኞ መስከረም 9 ያዘጋጀሁትን ዘገባ ለባልንጀሮቼና ለ ዶ/ር አበበ  ደሰኮርኩ:: የሳምባ ውስጥ እባጭ ሊያመጡ የሚችሉ በሽታዎችን የምችለውን ያህል ሰሌዳው ላይ ደረደርኩ:: በዲስኩሩ መጨረሻ ላይ እኔ እንደተለመደው በራሴ አልረካሁም: ዶ/ር አበበ ግን አቀራረአቤን በማድነቅ አፅናናኝ::