Sunday, July 9, 2017

ማክሰኞ ጥቅምት 13 1988 አ.ም.


ህክምና ትምህርት ሁሉ ስፋት ግዝፈትና ጥልቀት ዋና መገለጫ የውስጥ ደዌ ሕክምና (Internal Medicine) ነው:: የ Internal Medicine ሁለተኛ ዙር ትምህርታችንን ዛሬ ከዶክተር ጴጥሮስ ጋር በተደረገ የህሙማን ጉብኝት (Round) ጀመርን:: ባለፈው ሳምንት ደስ ባላለኝ መልኩ የተጠናቀቀው የቀዶ ሕክምና (Surgery) ትምህርት ያዞረው ናላዬ ወደነበረበት ገና አልተመለሰም:: ስለዚህም የዛሬውን Round በግማሽ አቅሌ ነው የተከታተልኩት:: ኢንተርኞቹ የሕሙማኖችን የምርመራ ውጤት እንዲሁም የህክምና ዝርዝር (Management Plan) ለዶክተር ጴጥሮስ ሲገልፁለትና በጉዳዩ ላይ ሙሉ በሙሉ ኃላፊነት ወስደው ሲወያዩበት: ሲከራከሩበት እኔ እነርሱን በአግራሞት እየተመለከትኩ በውስጤ ግን ፍርሃት ሲንሰራፋ ተሰማኝ:: ምክንያቱም የሚያወሩት ነገር ለኔ ባዕድ ሆነብኝ: ምንም የማውቀው ነገር የለም:: በሚቀጥለው ዓመት እኔም እንዲህ እንደነሱ ኢንተርን ስሆን አሁን እንደሚያደርጉት ማድረግ እችል ይሆን? ብየ ራሴን ጠየኩ:: ከባለፈው ሳምንት የፈተና ወቅት ሽብር ወጥቼ ሌላ ሽብር ውስጥ ገባሁ:: ጣጣ ነው:: አራተኛ ዓመት ላይ ያወኩትን በሙሉ ረስቼዋለሁ ማለት ነው......የተመደቡልኝን ህሙማን በሁዋላ ማነጋገርና መመርመር እንዳለብኝ ሳስበው ለራሴ ዘገነነኝ:: ዶክተር ጴጥሮስ ከረዥም ቁመናው: ቀላ ካለው ፊቱና በነጭ ሸሚዙ ላይ ካንጠለጠው ያማረ ከረባት የማልጠብቀው ቁጣና አዘቃዛቂ ስድቦች ያሉት ሰው ነው::  ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ኮሪደሩ ላይ እርሱኑ እየጠበቅን ስናወራ ገና ለመጀመሪያ ግዜ ያገኘን ቢሆንም ሰላም እንኩዋ ሳይለን “What are you guys doing here!?” በማለት በጅምላ ቀልባችንን ገፎ ከቆምንበት በታትኖናል::  በውስጤ ይህችን ሳምንት ከአስተማሪ ወቀሳና ስድብ ልትረፍ እንጂ ለሚቀጥለው ሳምንት አውቅበታለሁ አልኩ::
 ::

No comments:

Post a Comment