ማክሰኞ ጥቅምት 13 1988 አ.ም.
የህክምና ትምህርት ሁሉ
ስፋት ግዝፈትና ጥልቀት ዋና መገለጫ የውስጥ ደዌ ሕክምና (Internal Medicine) ነው:: የ Internal
Medicine ሁለተኛ ዙር ትምህርታችንን ዛሬ ከዶክተር ጴጥሮስ ጋር በተደረገ የህሙማን ጉብኝት (Round) ጀመርን:: ባለፈው
ሳምንት ደስ ባላለኝ መልኩ የተጠናቀቀው የቀዶ ሕክምና (Surgery) ትምህርት ያዞረው ናላዬ ወደነበረበት ገና አልተመለሰም::
ስለዚህም የዛሬውን Round በግማሽ አቅሌ ነው የተከታተልኩት:: ኢንተርኞቹ የሕሙማኖችን የምርመራ ውጤት እንዲሁም የህክምና
ዝርዝር (Management Plan) ለዶክተር ጴጥሮስ ሲገልፁለትና በጉዳዩ ላይ ሙሉ በሙሉ ኃላፊነት ወስደው ሲወያዩበት:
ሲከራከሩበት እኔ እነርሱን በአግራሞት እየተመለከትኩ በውስጤ ግን ፍርሃት ሲንሰራፋ ተሰማኝ:: ምክንያቱም የሚያወሩት ነገር ለኔ
ባዕድ ሆነብኝ: ምንም የማውቀው ነገር የለም:: በሚቀጥለው ዓመት እኔም እንዲህ እንደነሱ ኢንተርን ስሆን አሁን እንደሚያደርጉት
ማድረግ እችል ይሆን? ብየ ራሴን ጠየኩ:: ከባለፈው ሳምንት የፈተና ወቅት ሽብር ወጥቼ ሌላ ሽብር ውስጥ ገባሁ:: ጣጣ ነው::
አራተኛ ዓመት ላይ ያወኩትን በሙሉ ረስቼዋለሁ ማለት ነው......የተመደቡልኝን ህሙማን በሁዋላ ማነጋገርና መመርመር እንዳለብኝ
ሳስበው ለራሴ ዘገነነኝ:: ዶክተር ጴጥሮስ ከረዥም ቁመናው: ቀላ ካለው ፊቱና በነጭ ሸሚዙ ላይ ካንጠለጠው ያማረ ከረባት
የማልጠብቀው ቁጣና አዘቃዛቂ ስድቦች ያሉት ሰው ነው:: ከጥቂት
ደቂቃዎች በፊት ኮሪደሩ ላይ እርሱኑ እየጠበቅን ስናወራ ገና ለመጀመሪያ ግዜ ያገኘን ቢሆንም ሰላም እንኩዋ ሳይለን “What
are you guys doing here!?” በማለት በጅምላ ቀልባችንን ገፎ ከቆምንበት በታትኖናል:: በውስጤ ይህችን ሳምንት ከአስተማሪ ወቀሳና ስድብ ልትረፍ እንጂ
ለሚቀጥለው ሳምንት አውቅበታለሁ አልኩ::
::
No comments:
Post a Comment