Saturday, December 23, 2017

ህዳር 25 1988 አ.ም.

በዚህ ቀን ጠዋት የኔ ቡድን ያልጋ ዙሪያ ትምህርት (bedside) የነበረው ሲሆን አንዱም የቡድኑ አባል ትምህርቱ ጠዋት እንደሆነ ስላልነገረኝ ሳልገኝ ቀረሁ:: አመለጠኝ::  ለኔ ፕሮግራሙ ከሰአት በሁዋላ የሚካሄድ  ነበር የመሰለኝ:: እንደዚህ መቅረት  በጣም በጣም ነው የሚከብደኝ:: ጠዋት እኔ ተረጋግቼ አገር ደህና ብዬ ስረማመድ አምስት ሰዓት ተኩል ገደማ ተቧዳኞቼ በእውቀት በልፅገው ሲወጡ አየሁዋቸው:: ያለኔ መኖር  ይህ በመሆኑ ከመጠን ባለፈ ተበሳጨሁ : ሴራ መሰለኝ:: ሁሉንም  ለተወሰኑ ሰአታት ጠላሁዋቸው:: ክፉዎች!

በዚህ ቀን ምሽት ላይ በጣለው ዶፍ የቀላቀለ ዝናብ ምክንያት የኤሌክትሪክ አገልግሎት በመቁዋረጡና ለማንበብ የሚረዳ የመብራት አገልግሎት በመጥፋቱ የተከሰተውን ሰበብ በመንተራስ የቅርብ ጉዋደኞቼና የአስተሳሰብ ተጋሪዎቼ ከሆኑት አብይና አብርሃም ጋር በመሆን ከጤና ሳይንሱ ወረድ ብላ ከምትገኘው ቆጪ ሰፈር በመጠጥ ለመዝናናት ወረድን::  ሌላ ጉዋደኛችን ተከራይቶ ከሚኖርባት ሁለት ሜትር በሁለት ሜትር የምትሆን ትንሽ የኪራይ ቤት ውስጥ መሬት ላይ ተቀምጠን ከዚያው አካባቢ ያስገዛነውን ጠጅ እየጠጣንና የፍልስፍና ድባብ የተላበሰ ወግ እየጠረቅን አመሸን:: እኔ መቼም ከዚህ በፊት እንዳልኩት ከምወዳቸውና ሃሳብ ከሚጋሩኝ ጉዋደኞቼ ጋር የማሳልፈውን ግዜ በፍቅር ነው የማጣጥመውና  የምወደው:: ምንም እናርግ ምን ወይም ምንም አናርግ አያገባኝም ነገር ግን ከነዚህ ጉዋደኞቼጋ መሆንና ግዜውን አብሮ ማሳለፉ ብቻውን የሚሰጠኝ ደስታ አለ::  በዚያች እስር ቤት በምታህል ትንሽ ክፍል ቤት ውስጥ  በሻማ ብርሃን እየተያየን: ጠጃችንን እየጠጣንና በየተራ ምናባችን የሰነቀውን ፍልስፍናዊ ሃሳቦች እየተካፈልን እንዲሁም እያካፈልን እስከ ምሽቱ አምስት ሰዓት ቆየን::  ወደ ጤና ሳይንሱ ስንመለስ ደጁ በደማቅ ጨረቃ የተዋበ ነበር::  ጨረቃ ድምቡል ቦቃ.....


በበነጋው ወደተለመደ ትምህርት የተሞላ ባህር ውስጥ ገባሁ:: የውስጥ ደዌ ሕክምና ፈተና እየተቃረበ ስለነበር ትከሻዬን መክበድ አስቀድሞ ጀምሮኛል...........:: ትከሻ መክበድ ብቻ ሳይሆን ፈተና ሲደርስ አይኔም መርገብገብ ይጀምራል:: ግን ይህን ሁሉ ስለለመድኩት ምንም አይመስለኝም:: አንዳንዴ አንዳውም በዚህ ሁሉ ርካታ አልባ የህክምና ትምህርት የንባብ ሂወት ውስጥ እየተሰቃየሁ ይሆን እንዴ? ብዬ አስባለሁ:: እየተሰቃየሁ ቢሆን በውነቱ ላውቀው አልችልም:: የስሜት ህዋሳቶቼና የስሜት መሰማት አቅሜ ክፉኛ ስለቀነሱ አእምሮዬ የተለያዩ አጋጣሚዎችን ባንድ አይነት ሁኔታ መቀበል ከጀመረ ቆየ....

No comments:

Post a Comment