Sunday, January 31, 2016


ሐምሌ 1 ቀን 1985 አ.ም  ከምሽቱ 5 ሰዓት ከ 40 ደቂቃ
ባለፈው ሰኔ መጨረሻ ላይ በዋለው ቅዳሜ: በ 1983 አ.ም አብረውን ትምህርታቸውን ጀምረው የነበሩ የዲፕሎማ መረሃ ግብር ተማሪዎች ሁሉ ተመረቁ:: አንዳንዶቹ የቅርብ ጉዋደኞቻችን ነበሩ:: ስለዚህም ከነሱጋ በመለያየታችን ሆድ ባሰን:: ሰሞኑንም ጉዋዛቸውን ሽክፈው ግቢውን እየለቀቁ ነው......

በዚህ ቀዝቃዛ የክረምት ምሽት ላይ የተለመደውና በተደጋጋሚ ከመከሰቱ የተነሳ እንደወንድም ወይም እህት የተላመድኩት የኤሌትሪክ ኃይል መቁዋረጥ ተከስቶ ስለነበር ማጥናትና ማንበብ አይቻልም ነበር:: እሰይ!!! ስለዚህም በዚህ ትምህርታቸውን በትጋት ለሚከታተሉ መጥፎ ለኔ ግን ሸጋ በሆነ አጋጣሚ ከእመቤትና ፅጌረዳ ጋር ረዘም ያለ የእግር ጉዞ እያደረግን ተናፈስን:: አየሩ መቸም ቀዝቀዝ ያለ ቢሆንም ርጋታ የተላበሰ እንዲሁም ባፍንጫና ባፍ ሲምጉት የሆነ ደስ የሚል ነገር ይዞ ወደውስጥ የሚገባ ስነበር ተመችቶኛል:: ከሴቶቹ እንደተለያየሁ አራቱን ጉዋደኞቼንና የመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼን አብይ: መንግስቱ: ሚሊዮንና አምሳሉን አገኘሁዋቸው:: ከቅርብ ግዜ ወዲህ በተደጋጋሚ እንደምናደርገው ዛሬም ወደ ግሪን ሆቴል ሄደን እየጣንና እየተጨዋወትን አመሸን: ኡፍፍፍ...በቃ በጣም ነው ደስ ያለኝ:: እኔ ትምህርት ሳይሆን የሄን ነው የምፈልገው:: ከጉዋደኛጋ መሳቅ: መጫወት: መቦለት: ማውራት:መቃለድ: መቀለድ: እንደገና መሳቅ........ ወደ ጤና ሳይንሱ ስንመለስ የኤሌትሪክ ኃይል ወደቀድሞ ሁኔታው ተመልሶ ስለነበር አንዳንድ የጥናትና ፅሁፍ ግልበጣ ሥራ ላይ የተሰማሩ ግለ-ተማሪዎችን ማየት ይቻል ነበር::

ሐምሌ 3 ቀን 1985 አ.ም 
ዛሬ ጠንከር ያለ የሐምሌ ዝናብ አረንጉዋዴይቱን ጅማን ደበደባት:: ሐምሌ ሐምሌነቱን ለጅማ አሳወቃት:: መጣሁ: ያዥ እንግዲህ! አላት:: ጅማም ይህን ተቀብላ ክረምት ክረምት መሽተት ጀመረች:: ይበልጥ አረንጉዋዴ ሆነች::በየቦታው እሸት በቆሎ መታየት ጀመረ:: ሻይ የሚጠጣ በረከተ:: ወፍራም ልብሶች ተማሪዎች ላይ ፊጥ ብለው ይታዮ ጀመር:: የቤተ መፅሀፍቱ ሙቀት መቀነሻ ቬንትሌተሮች ስራቸውን አቆሙ:: ስለዚህም ቤተመፅሃፍቱ ውስጥ የርምጃና የመፅሀፍ ገለጣ ድምፆች በቬንትሌተሮቹ ዝዝ...ዝታ መሸፈናቸው ቀርቶ ይሰሙ ጀመር:: ጠዋትም ማታም አየሩ መቀዝቀዝ ጀመረ..........

እንደ አምናው የፊዚዮሎጂ ትምህርት በአንድ መስጠሊ ግብፃዊ መምህር የተነሳ ሊደብረኝ የሚሞክረውን የማይክሮባዮሎጂ ትምህርት እንዴት አድርጌ ቀልቤን እንደምሰጠው ግራ ገብቶኛል:: ሰውየው በጭራሽ አልጣመኝም:: ነካ ነካ ነው የማስተማር ዘዴው:: ከትምህርቱ በተጉዋዳኝ ከፍል ውስጥ በላይበላዩ ሲጃራ ያጨሳል::: እያንዳንዱን ሲጃራ አጭሶ ሲጨርስ እሳቱን የጫማው ሶል ላይ ያጠፋና ቁሩውን በመስኮት ወደውጭ ከወረወረ በሁዋላ ከያዘው ባኮ ውስጥ ሌላ አውጥቶ በላይተር ይለኩሳል:: ከዚህ በፊት አይቼ የማላውቀው ነገር ነው::

ባጠቃላይ ከሁለተኛ ዓመት ይልቅ የሻላል ብዬ የተማመንኩበት የሶስተኛ ዓመት ትምህርት ይባስ ብሎ ደረቅና የማይስብ እየሆነብኝ ነው::

ሐምሌ 5 ቀን 1985 አ.ም 

እኔና ጉዋደኛዬ ቤተማርያም ዛሬ ምሽት ላይ ተአምር በመሰለ ሁኔታ ከሌባ ጡጫና ዝርፊያ አመለጥን:: ነገሩ ባጭሩ እንዲህ ነው:: እኔና ቤተማርያም የዛሬውን የሌክቸር ሆልና የላይብረሪ ጥናታችንን አጠናቀንና አንድ ላይ ሆነን ወደ ዶርማችን ስንመለስ ወደ ዋይት ሃውስ ህንፃ የሚያመራው ቀጭን መንገድ ላይ በግምት ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ 45 ላይ ሁለት ሰውነታቸው ገዘፍ ያሉ ሰዎች ከፊትለፊታችን ወደኛ አቅጣጫ እየተራመዱ አለፉን:: ጨዋታ ይዘን ስለበር አላስተዋልናቸውም:: ሰላሳ ሰኮንድም ያህል ሳይቆይ ከበስተጀርባችን ከፍተኛ ጩኸት ሰማንና ፊታችንን ወደሁዋላ በማዞር ባለንበት ቀጥ ብለን ቆምን:: ወዲያውኑ ከየአቅጣጫው የጤና ሳይንሱ ዘበኞችና ሌሎች ተማሪዎች ወደ ተጮኸበት አቅጣጫ ሲሮጡ አየናቸው:: በትክክል እኛን አልፈው የሄዱት ግዙፍ ሰዎች ሌቦች ነበሩ ማለት ነው! እኔ በበኩሌ ካለሁበት ቆሜ ሌቦቹ ወደ በጨለማ ወደተሸፈነው ጫካው ውስጥ እየሮጡ ሲጠፉ ይታየኝ ነበር:: ማንም የተከተላቸው የለም: ያ አደጋ አለውና:: እኔና ቤተማርያም ከሁዋላችን የነበሩትና በሌቦች ጥቃት የተሰነዘረባቸው ተማሪዎች ባይኖሩ ኖሮ የነሱ እጣ ፈንታ የኛ ይሆን እንደነበር በማሰብ ተሸማቀቅን...ኡ

No comments:

Post a Comment