Sunday, January 10, 2016

ሰኞ የካቲት 15 ቀን ፩፱፰፭ አ.ም..ከምሽቱ 12 ሰዓት ከ 45 ደቂቃ

CBTP
የሁለተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርቴን በብቃት በማጠናቀቅ ፈተናዎቹን በሙሉ በማለፍ ለሶስተኛ ዓመት እንደታጨሁ ይፋ ሆነ:: የመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼም  ሆኑ ሌሎች እኔን መሰሎች ሁሉ አለፉ:: መግለፅ በሚያዳግት ሁኔታ ሁላችንም ደስ አለን:: ውጤታችን ይፋ ከሆነ በሁዋላ ታስረው እንደተለቀቁ እርግቦች ሆንን.... በጤና ሳይንሱ  ግቢ ውስጥ  ባሉት ረዣዥም  ዛፎች ላይ ወዲያና ወዲህ ከሚስፈነጠሩት ጉሬዛዎች ቀጥሎ እንደልባችን  የምንታይ  እኛ ሆንን:: በተከተሉት ቀናት በኛ ዶርም  ዉስጥ  ከሰዓት ከሰዓት መሰባሰብን ልማዳችን አረግነው:: በብዛት ሙዚቃ ይኖራል:: የመሀሙድ አህመድ የቆዩ እንዲሁም  የአስቴር አወቀ ለስላሳ ዘፈኖች ዋናዎቹ ናቸው:: እነዚህን እየሰማን የባጥ የቆጡን እናወራለን:: በፈተና ወቅት ሳንሰማቸው ያመለጡንን የአለምም ሆነ ያገር ወሬዎች ሰምተን የመረጃ ቁዋቶቻችንን እናድሳለን::

በነገራችን ላይ: በጅማ ጤና ሳይንስ የህክምና ትምህርት መረሃ ግብር መሰረት የአመቱ  ፈተና ካለቀና ውጤት ከተሰማ በሁዋላ ወደቤት መሄድ የለም! Community Based Training Program (CBTP) ላይ ለአንድ ወር መሳተፍ አለብን:: ይህ ሕብረተሰብ ተኮር የጤና ስልጠና የትምህርታችን አካል ነው:: በቡድን ተከፋፍለን ጤና ሳይንሱ በሚመድበን ቀበሌ በመሄድ በየቀኑ የተለያዩ ተግባራት እናከናውናለን:: በዚህ ዓመት የምንሰራው ሥራ በዋነኘት ከነዋሪው መረጃ መሰብሰብ ይሆናል:: ስለዚህም አስቀድሞ የተዘጋጁ ጥያቄዎችን ይዘን ከቤት ቤት እንዞራለን::


እኔ ያለሁበት ቡድን የተመደበው የጅማ ከተማ አካል የሆነ ነገር  ግን ዳርቻ ላይ ያለና ከፊል ገጠራማ ቀበሌ ውስጥ ነው:: ከቡድናችን ውስጥ በተለይ እኔና ኃይሉ የምንሰራበት ቦታ ደምበኛ ገጠር ነው:: እንዴት ይህ ቦታ በጅማ ከተማ ስር እንደሆነ ግራ ገብቶኛል:: በዚህ አካባቢ እኔና ኃይሉ መረጃ ለመሰብሰብ በምንዘዋወርበት ወቅት ያስተዋልኩት አንድና አንድ ነገር ቢኖር ባካባቢው የሚኖሩትን ሰዎች ስር የሰደደ ድህነት ነው:: ከዚህ በፊት ለእረፍት ወደ ራሴ የትውልድ ሰፈር ስመለስ ያስተዋልኩትን የነዋሪ ድህነት አስታውስኩ:: ይህ ግን እጅግ በጣም የባሰ ነው:: ገጠር በመሆኑ ብቻ በተፈጥሮ ቸርነት የዘሩትን ፍሬ ከመጠበቅ በስተቀር ሌላ ምንም ሃብትና ንብረት የሌላቸው ምስኪን ቤተሰቦች አየሁ:: አንዳንድ ቤተሰቦች ስምንትና ዘጠኝ የሚሆኑ ልጆች ያሉበት ሲሆን የዓመት ገቢያቸውን በምንጠይቃቸው ጊዜ የሚሰጡን መልስ "ከሶስት እስከ አራት ኩንታል በቆሎ" የሚል ነው:: ማመን ያስቸግራል..... እዚህ ገጠራማ የቀበሌ ከፍል የኤሌክትሪክ መስመር ሰንጥቆት ቢያልፍም በየቤቱ ግን የኤሌክትሪክ ኃይል የሚጠቀም መብራት የለም:: ስልክም የለም:: የዉሃ መስመር የሚባል ነገር የለም:: ይህ አጋጣሚ ለመጀመሪያ ጊዜ ስለ ሀገራችን ድህነት የበለጠ መረዳት ያገኘሁበት ይመስለኛል.....

No comments:

Post a Comment