Sunday, March 13, 2016

ነሐሴ 1985 አ.ም.

ለእረፍት ወደ አዲስ አበባ ለመሄድ በተዘጋጀሁበት ዋዜማ ምሽት በጅማ ሰማይ ላይ ታንፅባርቅ የነበረችውን ግማሽ ጨረቃ ምን ግዜም አልረሳትም:: ያይኔ ምግብ የሆነች የማታስከፍል ቆንጆ ድፍን ቀይ ጨረቃ..... ለምን እንደሆነ ባላውቅም ከዚህ ትውስታ ጋር ተያይዞ ያሳለፍኩት የሶስተኛ ዓመት የመጀመሪያው ሴሚስተር ጉዞ ውልብ ሲልብኝ በዚህ ውስጥ ደግም እመቤትን አስታወስኩ:: እመቤት አዲስ አበባ ዮሐንስ ቤተክርስትያን አካባቢ ያፈራት መልካም ሴት:: እመቤት ባለፈው ሴሚስተር ከመቼውም ግዜ በላቀ ከኔ: ከአብይና ከመንጌ ጋር: ቅርርብ ጨምራለች:: ብዙ ጊዜ እኛ ወደተሰበሰብንበት ትመጣና በደስታና በሳቅ ትቀላቀላለች:: በቃ ከኛ ጋር መሆን እየተመቻት እንደመጣ መገመት አያዳግትም:: ከተቀላቀለችን በሁዋላ እንደልቧ ታወራለች: ትስቃለች: ትጫወታለች: መራር የሆኑ ቀልዶቻችንን ትቃለዳለች:: አልፎ አልፎም ሚስጥር ታጫውተናለች:: የአብይና መንጌን አላውቅም እኔ ግን ከአህቶቼ በስትቀር ከተቃራኒ ፆታ ጋር አብሮ መዋል መጫወት ስላለመድኩ ነገሩ አዲስ ሆኖብኛል:: ይህን የምለው ግን ሁኔታው ለኔም እንደተመቸኝ ሳልክድ  ነው::

ነሐሴ 19  ቀን ጅማን ለቅቄና ባውቶቡስ ተፈናጥጬ አዲስ አበባ ቤቴ ደንገዝገዝ ሲል ደረስኩ:: አዲስ አበባ በሚሰነፍጥ ቀዝቃዛ አየር ተቀበለችኝ:: እዚህ አሁንም ድረስ ጠዋቱን ሙሉ ይዘንባል:: ከሰዓት ደግሞ ደነናማ ሆኖ በጣም ይቀዘቅዛል:: ውስጥንም ያቀዘቅዛል:: በነገራችን ላይ በዚህ የእረፍት ግዜ ግጥም ለመፃፍ እቅድ አለኝ::

ጳጉሜ 1985 አ.ም.
እነሆ 1985 ሊፈፀም የቀሩት ጥቂት ቀናት ናቸው:: ከዚያ በሁዋዋላ ያበሻው ፀደይ ወር መስከረም ብቅ ይላል:: መስከረምን በእውነት በጣም እወደዋለሁ:: ልጅነቴን የሚያስታውሰኝ ወር ነው:: አደይ አባባን ያስታውሰኛል:: ኩልል ያለ ውሃ የሚፈልቅባቸው ምንጮችንም ያስታውሰኛል:: ሰፈሩ መንደሩ ሁሉ አረንጉዋዴ መሆኑንም አይዘነጋኝም::  ከጉዋደኞቼ ጋር ሆነን በቀለም አይነትና በቁጥር የበዙ ቢራቢሮዎችን  ስናባርር ትዝ ይለኛል....

በወላጆቼ (በኛ) ቤት ውስጥ የዘመን መለወጫን ለማክበር የሚደረገው እንቅስቃሴ ከሌላው ግዜ የበለጠና ቀልቤን የሳበ ነው:: ለምን እንደሆነ አልገባኝም:: ላለፉት ጥቂት ቀናት ቤት ውስጥ የአውራ ዶሮ ድምፅና ኩኩሉ እየሰማሁ ነው:: ከጉዋዳ የሚወጣው የበዓሉ ለት የሚሰራውን ዶሮና ስጋ ወጥ ለማጣፈጥ ተብለው የተዘጋጁ ቅመማ ቅመሞች: በርበሬና ቅቤ ሽታ መቼም ለጉድ ነው:: እየበሰለ ያለ ጠላ ሽታም አልፎ አልፎ በነፋስ መልክ ወደ ሳሎን ቤት ይመጣል::

በነገራችን ላይ የኛ ቤት ማታ ማታ ሞቅ ይላል:: በየቀኑ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት አካባቢ ረዘም ያለ የቡና ስነስርዓት ይጀመራል:: ከእህቶቼ አንዷ ቡናውን የማዘጋጀት ኃላፊነት ትወዳለች:: ከሰል ይቀጣጠላል: ሰፊ ሮሆቦት ሳሎኑ መሃል ላይ ይሰየማል: ጀበና ይመጣል: ቡና ይቆላል: ፈንድሻም ይንዶሾዶሻል:: እጣንና ዑድ ይጨሳል:: በቡናው መሃል እራት ይቀርባል:: የቡናው ስርዓት ቢያንስ ሁለት ሰዓት ያህል የውስዳል:: በመሃል ቀልድ ሳቅ ጨዋታ ይደራል:: የቡናው ስነ ስርዓት ሲጠናቀቅም ቀስ በቀስ ሁሉም ወደየመኝታው ይሄዳል:: አባታችን ብቻ የራድዮኑን ጣቢያ እየቀያየረ የእንግሊዝኛ ወሬ ሲያዳምጥ ሌሊቱን ያጋምሳል:: እኔም ሳሎን ውስጥ ከተዘረጋልኝ ታጣፊ አልጋ ላይ ተንጋልዬ አብሬው በርቀት አዳምጣለሁ.....

No comments:

Post a Comment