Friday, March 31, 2017



መስከረም  26 ቀን 1988 አ.ም. ቅዳሜ ጠዋት

ህልሜ

በሠርጀሪ ፈተና መቃረብ የተነሳ ሰሞኑን ከመተኛቴ በፊት የእንቅልፍ ኪኒን (diazepam) እወስዳለሁ:: ታዲያ ለሽ ብዬ ነው የምተኛው:: እኔ ብቻ ሳልሆን ቁጥራቸው ቀላል የማይሰኝ ባልንጀሮቼ ያለሱ እንቅልፍ እንደማይወስዳቸው ውስጥ ውስጡን ሰምቻለሁ:: ብቻ ይህ የአደባባይ ጉዳይ አይደለም::

ታዲያ በእንቅልፍ ክኒኑ ይሁን ወይም በሌላ ምክንያት ትናንት ሌሊት ለዛሬ ሰፋ ያለና የሚገርም አይነት ሕልም ታየኝ:: የህልሙን እያንዳንዱን ድርጊት ቁልጭ ባለ መልኩ በማስታወሴ ነው ይበልጥ የተገረምኩት....

የቀዶ ጥገና ዲፓርትመንት ኃላፊ የሆነው ዶክተር አለምሰገድ ሌክቸር እየሰጠን ነበር:: የነበርንበት ክፍል ግን ከወትሮው ሌክቸር ሆል የተለየ ነበር:: ሴሚናር ከምናደርግባቸውም ክፍሎች የተለየ ነበር:: ከኔ ቡድን (group) የነበርኩት እኔ ብቻ ነኝ:: ሌሎቹ የት እንደነበሩ ትዝ አይለኝም:: የሆነ ሰው ዶክተር አለምሰገድን ውጭ ቆሞ እየጠበቀው ነበር:: ስለዚህም ዶክተር አለምሰገድ ሌክቸሩን ለማሳጠር በፍጥነት እየተናገረ ነበር:: በእጁ የሲጋራ መለኮሻ ላይተር ይዞ ነበር:: ድንገት ግልፅ ባልሆነልኝ ምክንያት ላይተሩን ለኮሰው:: በዚያው ቅፅበት ከላይተሩ ጫፍ የሚስፋፋ ነጭ ሰማያዊ ጭስ መውጣት ጀመረ:: እኔ ካርቦን ሞኖክሳይድ ነው ብዬ አሰብኩ:: ወይም ሌላ ለሂወት የሚያሰጋ ኬሚካል መሰለኝ:: ክፍሉ ውስጥ የነበረ ተማሪ በሙሉ በያቅጣጫው ሂወቱን ለማትረፍ መራወጥ ጀመረ:: አንዳንዶቹን በጭሱ ታፍነው የክፍሉ ወለል ላይ ሲወድቁ ተመለከትኩ:: ዶክተር አለምሰገድ የት እንደደረሰ አላውቅም:: እኔም ራሴ ትንፋሽ የማጠር ስሜት ይሰማኝ ጀመር::  ባለሁበት ድካምና ጡንቻዎቼ ሲዝሉ ተሰማኝ:: ከየት እንደመጣ ያላወኩት አንድ ሕፃን ልጅ ጋር ከክፍሉ ለመውጣት የምንችለውን ያህል ተፍጨርጭረን መጨረሻ ላይ ተስካልንና ወጣን:: ከዚያም ሩጫዬን ከልጁጋ አብሬ ቀጠልኩ:: ከክፍሉ እንደወጣን ከፊት ለፊታችን ያጋጠመን በረጃጅም የእህል ማሳ ነበር:: ወደማሳው እየሮጥን ገባንበትና በውስጡም ሁነን ሩጫችንን ቀጠልን:: በማሳው የወድያኛ ጥግ ደርሼ አልፌው ስወጣ አብሮኝ የነበረው ልጅ የለም: ብቻዬን ነበርኩ:: ከፊት ለፊቴ መንደር አየሁ:: በአንድ አይነት ሁኔታ የተሰሩ ቤቶች አየሁ::  ቤቶቹ ነጫጮች ሲሆኑ በልጅኔቴ የተማርኩበት ቅዱሥ ጳውሎስ ትምህርት ቤት ግቢ ውስጥ ቀሳውስት ይኖሩባቸው የነበሩ ቤቶችን ይመስላሉ:: ወደቤቶቹ አቅጣጫ እያመራሁ ሳለ አንዲት ኮረዳ በድንገት መንገዱ ላይ  ብቅ ብላ አናገረችኝ:: እኔም በሌክቸር ሆሉ ውስጥ የተፈጠርውን ነገርኩዋት:: እርሱዋም ለደህንነቴ በማሰብ አዳሬን በመንደሩ እንዳደርግ መከረችኝ:: ይህን ካለችኝ በሁዋላ ወዴት እንደሄደች አላውቅም:: እኔ ግን ርምጃዬን ቀጠልኩ:: በመንደሩ ውስጥ ስጉዋዝ በመንገዱ ግራና ቀኝ ትልልቅ አለቶችን የሚፈልጡና የሚጠርቡ ሰዎችን አየሁኝ:: ካለሁበት ቆሜ ወደፊትለፊቴ  ስመለከት በርቀት የረጃጅም ህንፃዎች ጫፎች አየሁ:: ጂማ እንደነዚህ አይንት ፎቆች አይቼ አላውቅም:: ካለሁበት ወደየት እንዳመራሁ ትዝ አየለኝም ግን ሕልሙ እዚያ ላይ አለቀ...........


No comments:

Post a Comment