Sunday, June 25, 2017

የሰርጀ   ፈተና ሰሞን

እሁድ መስከረም 27 1988 አ.ም.

በዚህ እለት ጠዋት ድብርት ተጫጭኖኝ የነበረ ቢሆንም ከሰዓት በሁዋላ ግን ከቅርብ ወዳጆቼ በተደረገልኝ የቂማ (ጫት) ግብዣ ምክንያት ንቃትን ተላብሼ ነበር:: በሰርጀሪ ፈተና መቃረብ ያደረብኝ ስጋት እንዳለ ሆኖ ጫቱን ግን አጣጣምኩት:: ነቃሁበት! ምሽት ላይ ጥይት ሆንኩና ወደሆስፒታል መሄድ አማረኝ:: ሕሙማኖቼን መጎብኘት አሻኝ:: እናም ወደ ዋርድ ሄድኩ:: እዚያ ስደርስ ዶክተር ሚናስን  አየሁት:: ተረኛው ቀዶ ሀኪም እሱ ነበር:: እሱም ጥይት ሆኖ ነበር:: በዶክተር ሚናስ ዙሪያ ግርግር ነገር አየሁ:: በመጀመሪያ ለምን እንደሆነ አላወኩም ነበር በሁዋላ ግን አንድ በመኪና አደጋ ደረቱና ሳምባው የተጎዳ ህመምተኛ እንዳለ ተረዳሁ:: ዶክተር ሚናስ ለዚህ ሰው ደረት-ቱቦ (chest tube) አስገባለት:: እኔና በዚያ የነበሩ ሌሎች ታታሪ የህክምና ተማሪዎች የደረት ቱቦ አገባብ ተመለከትን:: የሚገርመው ግን ዶክተር ሚናስ ስለደረት ቱቦ ወይም ስለ ደረት ጉዳት ይነግረናል ብዬ ስጠብቅ የሌላ ራስ ቅሉ ላይ የጦር ጉማጅ የተሰካበት ህመምተኛ ኤክስ ሬይ ይዞ የነበረ ሲሆን ስለ head injury ሰፊ ትንተና አደረገልን:: በራስ ቅል ጉዳት (Head Injury) ዙሪያ ሰፊና ጠቃሚ እውቀት አስጨበጠን:: ቅሟል እንዴ?  ከዶክተር ሚናስ ትንተና በሁዋላ ወደ ምድብ አልጋዎቼ ሄድኩ:: አንድ አዲስ ህመምተኛ ነበረኝ:: እሱም በመኪና አደጋ ነው የመጣው:: ቀኝ ክንዱ ላይ ያለው ጡንቻ ተቦጭቁአል (Avulsion):: ለነገ ጠዋት ራውንድ የሚሆነኝን ያህል መረመርኩትና ወደ ዶርም ተመለስኩ....

አርብ ጥቅምት ሁለት ቀን 1988 አ.ም.

ዛሬ ቅር ያለኝ ነገር አለ:: የቀዶ ጥገና ረዳት መምህር የሆነው ዶክተር አብርሃም በእሳት የተቃጠለ (Burn) ህመምተኛ ላይ ያልጋ ዙሪያ ውይይት (Bed Side) እንደሚያደርግ ታቅዶ የነበረ ሲሆን እኔም ሆንኩ የኔ ቡድን አባላት ስለ Burn አንብበንና ለጥያቄ ራሳችንን አዘጋጅተን ነበር:: ነገር ግን ዶክተር አብርሃም ሆን ብሎ ይሁን በሌላ የተመደበውን ሰዓት ስለ አንጀት እጢ (Colon cancer) በማውራት ገደለው:: የሚገርመው ስለ አንጀት እጢ ማውራቱ ሳይሆን ሆን ብሎ ነው ሊያስብለኝ በቻለ መልኩ የማናውቀውንና ትኩረት መስጠት የማይገባንን እንዲሁም በልካችን ያልሆነ  ነገር ነበር የሚያወራው:: እርግጠኛ ነኝ ያወራው ነገር ለፈተናም ሆነ ለተግባር አይጠቅምም:: ቅር መሰኘት ብቻ ሳይሆን እኔ ውስጤ ቅጥል ብሎ ነበር:: ለምን እንዲህ አደረገ ብዬ ራሴን ስጠይቅ የመጣልኝ ብቸኛው ግምት አብረውን Bed Side ሊካፈሉ የመጡ የ Nursing ተማሪዎች ስለነበሩ በነሱ ፊት ከኛ ከሕክምና ተማሪዎቹ እጅግ የላቀ እውቀት እንዳለው ላማሳየት ፈልጎ ይሆናል የሚል ነው:: ነው ደሞ!
በነገራችን ላይ ሌላም ቅር ያለኝ ነበር ዛሬ:: እናቴ በየወሩ የምትልክልኝን ሃምሳ ብር ዛሬ ጠብቄ የነበረ ቢሆንም ሳትልክ ቀረች::

እሁድ ጥቅምት 4  1988 አ.ም. ከቀኑ አስር ሰዓት

ሰርጀሪ የተግባር (Practical) ፈተና  ነገ ሰኞ ይጀመራል:: የኔ የፈተና ቀን ግን ሮብ ነው:: እንደተለመደው በዚህ የተግባር ፈተና ዋዜማ እለት በውስጤ ሽብር የነገሰ ሲሆን በራስ መተማመኔ ደግሞ ባይ ባይ ብሎኝ ሂዷል:: በርካታ ይህን አይነት የአእምሮ ውጥረትና የስሜት ልሽቀት የሰፈነባቸው ቀናት አሳልፊያለሁ ነገር ግን ልለምደው አልቻልኩም:: ሁልግዜ እንደአዲስ ነው:: በተለይ በተለይ የማልረሳው የሁለተኛ ዓመት (ፒሲ-ዋን) የመጨረሻ ቀን የፊዚዮሎጂ የቃል ፈተና ልፈተን አምስት ደቂቃ ሲቀር የተሰማኝን ስሜት ነው:: አሁን ለማመን በሚያስቸግረኝ ሁኔታ የልቤ ምት ጠፍቶብኝ ነበር:: በተለምዶ ሰው ሲደናገጥ የልቡ ምት ይበልጥ ይሰማል:: የኔ ግን ጠፋ:: የልቤን ምት እንደገና መስማት የጀመርኩት ስሜ ተጠርቶ ፈታኞቹ ወደነበሩበት ቢሮ ስገባ ነው:: ለማንኛውም አሁን የአምስተኛ ዓመት የቀዶ ጥገና የውስጥ (Internal) የተግባር ፈተና ነው ይሄ:: ማለቴ ገና ዓመቱ መጨረሻ ላይ የውጭ (External) ፈተና ይኖረናል:: የውስጤ መሸበር ግን እንደተጠበቀ ነው:: ባጠቃላይ ለፈተናው ዝግጁ አይደለሁም:: ደግነቱ ይህ የውስጥ ፈተና ሲሆን የውስጥ ስሜቴን ደሞ ማንም አያውቅም::  በሚቀጥሉት ተቂት ቀናት ውስጤን ለማረጋጋት ይረዳል ብዬ ያሰብኩት ስልት (ስትራቴጂ) የሚከተለው ነው:: አርስቱ የሰነፍ ተማሪ አቁዋራጭ ስልት ብለው ደስ ይለኛል::

  1. በምንም አይነት መፅሐፍ (Text Book) ከማንበብ መቆጠብ
  2. ደብተሮችንና ማስታወሻዎችን በፍጥነት ማንበብ::  የበሽቶች አናቶሚና ፊዚዮሎጂ ላይ ግዜ አለማባከን: ቀጥታ ወደጉዳዩ ገበመግባት ሕክምና: ላቦራቶሪ: የበሽታው መዘዝ (complications)ና ለበሽታው የሚያስፈልገው የቀዶ ጥገና ሕክምና የተመለከቱት ላይ ማተኮር::
  3. አላስፈላጊ ናቸው ብለህ ያሰብካቸውንና ሲነበቡ ደስ የማይሉ እንዲሁም ለመረዳት ቀላል ያልሆኑ ሀቆችን (facts) ዝለላቸው::
  4. ያልጋ ዙሪያ (Bed Side) ትምህርት ላይ የከተብካቸውን ማስታወሻዎች አንብብ::
  5. በምታነብበት ግዜ ህመምተኛውን አስብ::
  6. በምታነብበት ግዜ መፃፍ አቁም::
  7. ዛሬ ማታ ለማንበብ ይመቹኛል ወይም አስፈላጊ ናቸው ብለህ ያመንክባቸውን አርስቶች ምረጥ::
  8. መልካም ዕድል::

ልብ በል/ይ በዚሁ ቀን ምሽት ላይ በጥናት ሳልተጋ ቆይቼ ከምሽቱ አምስት ሰዓት ሲሆን መኝታ ክፍላችን ውስጥ ካለው ጠረጴዛ አጠገብ ቁጭ ብልም ቀን ለራሴ ቃል የገባሁትን ከላይ ቁጥር ሰባት ላይ የሰፈረውን ዘልዬው ወደ አልጋዬ አመራሁ ......


No comments:

Post a Comment