Wednesday, October 1, 2014

የብላቴ ማስታወሻ ማጠቃለያ

ዛሬ....
"የቤተሰብ ሃላፊነት ና የጎልማሳ ዳተኝነት ተባብረው ማስታወሻዬን እዚህ ብሎግ ላይ እንዳላሰፍር አርገውኝ ነው ሳልጽፍ የዘገየሁት!" በማለት የዛሬውን ጽሁፍ እጀምራለሁ።

ባለፈው የመስክ ላይ ፍንዳታ ና የአንድ አየር ወለድ ጉዳትን የሚያትት ጽሁፍ ካሰፈርኩ በኋላ በተከተሉት አራት የሚጠጉ ወራት ምንም አይነት ማስታወሻ አላሰፈርኩም። ለምን የሚለውን መመለስ አሁን ያዳግተኛል። በአራቱ ወራት ውስጥ በኔ የግል ሂወት ላይ እምብዛም የሆነ ለውጥ ባይከሰትም (ከጉርምስና መቀጠል በስተቀር) ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን የለውጥ ኩነት ግን አብዛኛው የዚህ ጽሁፍ ታዳሚ ያስታውሰዋል የሚል ግምት አለኝ።

ግንቦት 1983 አ.ም. አጋማሽ ላይ ብላቴን ይጎበኛሉ እንዲሁም ስልጡን ተማሪዎችን ይመርቃሉ ተብለው የተጠበቁት ሊቀመንበር መንግስቱ ከኢትዮጵያ መኮብለላቸውን በሬዲዮ ሰማን። ያንን ሶስት ሰአት የፈጀ ንግግር ባደረጉ በወሩ እንደማለት ነው። የሳቸውን መኮብለል ተከትሎ ከጥቂት ቀናት በኋላ በተተረማመሰ ሁኔታ ና ከተወሰኑ በአውቶቡስና በአይሮፕላን ግቢውን ከለቀቁ ተማሪዎች በስተቀር ሌሎቻችን በእግር ብላቴን ለቀቅን። በግምት 60 ኪሎ ሜትር የሚሆን የገጠር ፒስታ መንገድ የምጻተ እስራኤል በሚምስል ረጅም ሰልፍ አቋርጠን ሞርቾ የምትባል ከተማ ብሎም ወደ ሰሜን 25 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኘው አዋሳ አመሻሽ ላይ ገባን። ለዚህ የፈጀብን 24 ሰአት ይሆናል- በእርግጥ ለሁለት ሰአት የሚሆን አንዲት ትንሽ ከተማ ላይ ተኝተናል። እኔና ጓደኞቼ አንድ ላይ ነበርን። መንጌ፣ ሚሊዮን፡ አባይ፡ አብይና ሚፍታህን አስታውሳለሁ።

ኢሃዲግ ግንቦት ሃያ አዲሳበባ ሲገባ እኛ አዋሳ ነበርን። አዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዶርሚቶሪዎቹን ከብላቴ ለሚመለሱ ተማሪዎች ክፍት አርጎ ነበር መሰለኝ.. እዚያ ነበር የምናድረው። በዚያን ግዜ አዋሳን ምናልባትም መላው ደቡብን ምንም የሚያስተዳር መንግስት አልነበረም። እስከማስታውሰው ድረስ ግን ከጥቃቅን የመንግስት ሱቅና መጋዘን ዘረፋ በስተቀር ብዙ ግርግር አዋሳ ውስጥ አልነበረም። እንደውም የተወሰኑ የአካባቢ ሽማግሎችና ፖሊሶች ተሰባስበው በመኪና እየዞሩ ህዝቡን ሲያረጋጉ ትዝ ይለኛል። እኛን ከብላቴ የመጣነውን ተማሪዎች በየቀበሌውው የሚገኙ፡ሴቶች በመተባበር ምግብ አዘጋጅተው እንደመገቡን አስታውሳለሁ። እግዚአብሄር ይስጣቸው። ከጓደኞቼ ጋ አንድ ሳምንት ገደማ አዋሳ ቆይተን በአንድ አውቶቡስ ተሳፍረን ወደ አዲስ አበባ ቼ አልን፡ ከሚልዮን በስተቀር። እርሱ ቀደም ብሎ አንድ ከአዋሳ ወደ ሞያሌ የሚንቀሳቀስ የጭነት መኪና ላይ ተንጠልጥሎ ሲሄድ ታይቷል። እኛ ወደ አዲስ አበባ ባቀናንበት እለት የወያኔ ወታደሮች በ ወታደራዊ የጭነት መኪኖች ታጭቀው ወደ አዋሳ አቅጣጫ ሲያመሩ ተመልክቻለሁ። እስከዚያ ቀን ድረስ አዋሳ አልነበሩም።

ሁላችንም በሰላም አዲስ አባባ ደርሰን ወደየቤታችን ገባን። በማግስቱ በቅሎ ቤት የሚገኘው መሳሪያ ግምጃ ቤት ፈነዳ። ከዚያም ብዙ ብዙ ሆነ..........

ምንም እንኳን እንዘምትበት ና እንወጋው ዘንድ ታስበን የነበረ መሆኑን ቢያውቅም ደጉ የኢሃዲግ መንግስት ብላቴ የዘመቱም ሆነ ያልዘመቱ ተማሪዎች ሁሉ ያቋረጡትን ትምህርት በመስከረም ወር 1984 አ.ም. እንደገና እንዲቀጥሉ በጎ ፈቃዱ መሆኑ ሳያንስ ከብላቴ ለተመለስነው በነፍስ ወከፍ 137 ብር እንደሰጠን አስታውሳለሁ...

በሚቀጥለው ማስታወሻዬ ጅማ ጤና ሳይንስ ተመልሰን ትምህርታችንን ከቀጠልንበት ከጸደዩ ከመስከረም ወር ጀምሮ የነበሩትን አንኳር አንኳር ክስተተቶች አሰፍራላሁ።፡ለዛሬው ደህና እንሰንብት.....

No comments:

Post a Comment