Thursday, December 11, 2014

ህዳር መጨረሻ ገደማ አስራ ዘጠኝመቶ ሰማንያ አራት ..
ካባለፈው የአውቶቡስ ተራ አጋጣሚ በሁዋላ በተሰማኝ ድንጋጤ ስርዓት ይዤ ትምህርቴን የምቀጥል መስሎኝ የነበረ ቢሆንም ፈፅሞ በጥናት ልተጋ አልቻልኩም:: ከፍተኛ የሆነና ስር የሰደደ የጥናት ፍላጎት ማጣት ውስጥ ገባሁ:: መማር ራሱ አዙሪት ነገር ሆነብኝ:: አለርጂክ! ይህን ከመረዳት የመነጨ ጭንቀት በአምሮዬ በየቀኑ ይመላለስ ገባ:: ቤተ ክርስትያን መሄድ: መፅሐፍ ቅዱስ ማንበብ እንዲሁም ማስታወሻ መፃፍ ጭንቀቴን የሚያቃልል አልሆነም:: የሚገርመው ግን ቀስ በቀስ ጭንቀቱን ለመድኩት:: ከዚያማ የሚያስጨንቀው አለመጨነቅ ሆነ…….ይገርማል

ወደቤት መመለሻዬ ተቃርቡዋል:: የሁለተኛ ሴሚስተር ፈተና ከጥቂት ሳምንታት በሁዋላ ተፈትነን አመቱን እናጠናቅቃለን:: የቤተሰቤን ሁኔታ ለጊዜው አላውቅም:: መልክትም ሆነ የኪስ ገንዘብ ከተላከልኝ ሰነበተ:: ነገር ግን እግዜር ይመስገን: ቢያንስ አባቴ ከእስር ቤት ተፈትቱዋል::

ከምሽቱ አራት ሰዓት በሁዋላ ለጥናት መቆየት ስላቃተኝ ሌሊት ሌሊት አስር ሰዓት ላይ እየተነሳሁ ማንበብ ጀምሪያለሁ:: እየሰራ ያለ ፕላን ይመስላል:: ይህ የጠዋት ሰዓት አእምሮዬ የመጨረሻ ብሩህ ደረጃ ላይ የሚሆንበት ሰዓት መሆኑን ከተገነዘብኩ ውዬ አድሬያለሁ:: እናም ሰሞኑን በዚህ ሰዓት የማነበው ከባዱና ዘግኛኙን Organic Chemistry ነው:: Sociology የሚባለውን ትምህርት አለማንበብ ብቻ ሳይሆን ክፍል ገብቼ የሚሰጠውን ሌክቸር እንኩዋን መከታተል ትቻለሁ:: 



ታህሳስ ስድስት አስራ ዘጠኝመቶ ሰማንያ አራት ..

መልካም ዜና:: አባቴ የማስተማሩን ሥራ እንደገና መጀመሩን በቅርቡ ለእረፍት ወደ አዲስ አበባ ሂዶ የተመለሰው የሰፍሬ ልጅ ታጠቅ ነገረኝ:: እህቶቼና ወንድሜም ትምህርታቸውን በሰላም እየተከታተሉ መሆኑን ተረዳሁ:: ታጠቅ እረፍት ላይ ሳለ ወደኔ ቤተሰቦች ቤት ብቅ ብሎ ነበር:: ወደ እረፍቱ ሲሄድ እኔ የፃፍኩትን ደብዳቤ አድርሶ ከነሱ ደግሞ ደብዳቤ: ጥቂት ገንዘብ: ዳቦ ቆሎና ሳሙና ይዞ ተመለሰ:: የቤተሰቡ አባላት: የመጨረሻዋ እህቴን ጨምሮ ደብዳቤ ፅፈው ልከዋል::ቤተሰቤ በደህና ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ በማወቄ በእውነት በጣም ደስ አለኝ:: ቀለለኝም:: በዚህ ቀን ለሁለተኛው ሴሚስተር ማጠቃለያ ፈተናችን የቀረው ሁለት ሳምንት ብቻ ነው:: ጥናት ተጧጧፏል:: ከባዮሎጂ Genetics: Plant Physiology: ከሂሳብ The Theories of Calculus: ከፊዚክስ Thermodynamics: Relativity ፈተና ውስጥ በዋነኝነት እንደሚካተቱ ተነግሮናል:: ብዙ ተማሪዎች ሳይተኙ እስከ ሌሊቱ ስምንት ሰዓት እንደሚቆዩ ለማየት ባልታደልም ሰምቻለሁ:: እኔ ይህችን አጭር ማስታወሻ ፅፌ ለመትኛት ስዘጋጅ ሰዓቱ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ከሃምሳ ዘጠኝ ደቂቃ ይላል…..

No comments:

Post a Comment