Friday, January 30, 2015

ሚያዚያ 10 ቀን 1984 አ.ም.
ጅማ


PC-1 እየተባለ የሚጠራውን የሁለተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርቴን ለመከታተል ጅጤሳ ከተመለስኩ ሁለት ሳምንት ሆነኝ:: የቅርቤ ከሆኑት ጉዋደኞቼ ጋር በዋይትሃውስ ዶርም ቁጥር 207 ውስጥ ከትሜያለሁ:: በርካታ የባቼ ልጆች ከእረፍት መልስ የወፈሩና ያማረባቸው ሲሆን እኔና ጥቂት ሌሎች ልጆች አላማረብንም ባይባልም የሰውነታችን ሁኔታ ለውጥ ሳያሳይ ነው የተመለስነው::

የፒሲዋን ትምህርቶች ለህክምና መሰረታዊ የሆኑትን ሳይንሶች Anatomy: Physiology: Biochemistry: Histology ና Embryology ያካተቱ ናቸው:: የአጠቃላይ ዲፓርትመንቱ ኃላፊነት የተሰጠው ሰው አቶ ኢሳያስ ይባላል:: አቶ ኢሳያስ ከቢሮ ኃላፊነቱ በተጨማሪ የBiochemistry እውቀት የታጠቀ እንደሆነና እንደሚያስተምረን በመጀመሪያው ቀን orientation ስብሰባችን ላይ ነግሮናል:: የፒሲዋን ትምህርቶችን መጪውን ዓመት ሙሉ ተቀምጠን የምናዳምጥበትና የምንቀስምበት ክፍል ውስጥ ወስዶ በመንፅሩ የበታች ዳርቻ አሻግሮ እየተመለከተን ረዥም ዲስኩር አደረገ:: ወፈር ያለ ሰውነቱና ጠቆር ያለ ገፅታው በመጀመሪያ ሳየው የሌላ አፍሪካ አገር ዜጋ እንዲመሰለኝ አርድርጎኝ ነበር::

አቶ ኢሳያስ በኦርየንቴሽኑ ወቅት ከተናገራቸው በርካታ ማስፈራሪያ መሰል አረፍተ ነገሮች መካከል አንድ በጣም የወደድኩለት አባባል አለ:: “በምንም ተአምር ከምሽቱ ስድስት በሁዋላ እንዳታነቡ: ዋጋ የለውም!” እኔ ታዲያ በሆዴ አርጎት ነው!? አልኩ ይህን ስሰማ:: ሌላው ደስ ያለኝ ነገር የፒሲዋን ትምህርቶችን የሚያስተምሩን እንደፊቱ ኩባውያን ሳይሆኑ ግብፃውያን እንደሚሆኑ መስማቴ ነው:: ከኛ የቀደሙት በኩባውያን የተስተማሩ ባቾች እንደነገሩን ከሆነ ከኩባውያን እንግሊዝኛ አለመቻል ጋ የተያያዘ ብዙ የመማር ማስተማር ሂደት ችግር ነበር:: ስለዚህም ተማሪዎቹ ለእውቀታቸው መዳበር ላይብረሪ ሂዶ መፅሐፍ ማንበብን እንደዋነኛ ምንጭ አድርገው መትጋትና መፍጋት ነበረባቸው:: እኔ ታዲያ በከዚህ በፊት ታሪኬ እንደገለፅኩት ቤተ መፅሐፍት ተቀምጦ ማንበብ ላይ ያለኝ ስር የሰደደ አሉታዊ አመለካከት በኩባውያን መምህራን ስር ብሆን ችግር መፍጠር ብቻ ሳይሆን ስጋት ውስጥ ይጥለኝ እንደነበር ግልፅ ነው:: ስለዚህም ግብፆቹ በእንግሊዝኛ ቁዋንቁዋ እንደሚያስተምሩን ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ባልሆንም የኩባዎቹ ካካባቢው መጥፋት ግን የአእምሮ ረፍት ሰጥቶኛል:: መቼም ግብፃውያኑ በአረብኛ እናስተምራችሁ እንደማይሉ ተስፋ አደርጋለሁ:: 

የሚገርመው ግን ፒሲዋን ከተጀመረ ሁለት ሳምንት ቢሆንም ግብፆቹ ገና አልመጡም:: ወሬያቸውም የለ:: አንዳንድ ወጣት ሀበሻ መምህራን ግብፆቹ እስከሚመጡ በሚል ለማስጀመር ያህል ሌክቸር እየሰጡን ቢሆንም ጥናት የሚባለውን ነገር የምር ለመጀመር ግን ያሚያነሳሳ ሞራል ገና አላበጀሁም: እኔ በበኩሌ:: የሌላውን አላውቅም::

1 comment:

  1. ሳሚ፤ በኩባዎቹ ባለመማርህ ብዙም የእረፍት ስሜት አይሰማህ፡፡ እድሜ ለነሱ - እንኳንስ ተነቦ ተቃጥሎ የማያልቀውን ሪፈረንስ መፅሀፍ ሁሉ ከገፅ እስከ ገፅ እንድንወጣው አንዳንዱም እንደ ዳዊት እንዲደግመው አድርገውናል፡፡

    ReplyDelete