Saturday, January 10, 2015

ጥር 23 ቀን 1984  .

አዲስ አበባ ቀራንዮ

የጥምቀት በዓል ባለፈው ሰሞን ተከበረ:: ይህ በዓል ሲከበር እዚህ ያደኩበት ሰፈር በመሆኔ በእውነት ደስ ብሎኛል:: የጥምቀት በዓል ልጅነቴን ጉልህ አድርገው ከሚያስታውሱኝ ትዝታዎች አንዱ ነው:: በልጅነቴ በየዓመቱ ጥምቀት ሲመጣ ጥምቀተ ባህር እየተባለ  ወደሚጠራ ስፍራ ከሰፈር ጉዋደኞቼ እንሄዳለን:: እዚያም ከዋዜማው እለት ጀምሮ ስንሮጥ: ስንላፋ እንዲሁም ለጥምቀት ብለን ባጠራቀምነው ሳንቲም ብርቱካን: በረዶ: ሸኮራ አገዳ: ብስኩት ወዘተ...እየገዛን ስንበላ ውለን እናመሻለን:: ጧፍ እናበራለን:: እንደሌላው ጊዜ ሳይሆን ለጥምቀት እለት እስከ እኩለሌሊት እንድናመሽ በወላጆቻችን ይፈቀድልናል:: መቼም የልጅነት ጉልበት ያማይልቅበት ነውና ጥምቀተ ባህር ውስጥ በአዋቂዎች እግር ስር ስንሹሎኮሎክና ካንዱ ጫፍ ወደ አንዱ ጫፍ ስንሮጥ አይደክመንም ነበር:: አንዳንድ ጉዋደኞቼ በእርግጥ የሚሮጡት ከሌላ ደከም ካለ/ ልጅ ላይ ብርቱካን ወይም ማስቲካ ወይም ሌላ የሚበላ ነገር መንትፈው ነበር::የቀራንዮ መድኃኔዓለም ታቦት ወደ ጥምቀተ ባህሩ ለጥምቀት ዋዜማ ለት ሲገባና በማግስቱም ከጥምቀተ ባህሩ ወደ ቤተክርስትያኑ ሲመለስ በሚጉዋዝበት ባቡር መንገድ ላይ የነበረው ትእይንት ፈፅሞ አይረሳኝም:: ባንድ ወገን የቤተክርስትያን ዘማሪዎች በቀለማት የደመቀ አንድ አይነት ልብስ ለብሰው  እስከቻሉት ድረስ በመጮህ ከበሮ በመደለቅ ሲዘምሩ ና አንዳንዶቹም ሲዘሉ: እልፍ ብሎ ደግሞ የብሄረሰብ ባህላዊ ጭፈራዎች የሚታዩበት ስብስብ (በተለይ ዶርዜኛ ና ኦሮምኛ): ከዚያ ደግሞ ዘመናዊ ሙዚቃ ሃርሞኒካ የሚዘፈንበትና ወጣቶች የጊዜውን ዳንስ የሚደንሱበት ግሩፕ የሚፈጥሩት የመንገድ ላይ ግርግር እስከዛሬ ባይነ ህሊናዬ አለ:: ዘንድሮ ይሄው አድጌ ወጣት የኮሌጅ ተማሪ ደንብ ደርበብ ብዬ ጥምቀትን ከዳር ቆሜ እንደ ትርኢት አየሁት:: የሀይ ስኩል ጉዋደኛዬና ጎንደር  ሕክምና ትምህርት ቤት የተመደበው ከፈለኝ አብሮኝ ነበረ::  ያኔ እኔ ራሴ ተዋናይ የነበርኩበትን የጥምቀት በዓል ተውኔት እንደ ታዳሚ ተመለከትኩት:: የጥምቀት በዓል ደስ ይላል....

ወደዛሬ ልመለስ:: ዕረፍቴ ረዥም ስለሆነ አንዳንዴ መታከት ብቻ ሳይሆን የምሰራው ግራ ግብት ይለኛል:: ልቦለዶች በተከታታይ እያነበብኩ ነው:: አንድ የተገነዘብኩት ነገር ቢኖር የትርጉም መፅሀፍት በብዛት እየተፃፉ ነው:: ልክ አሁን “Madam X ወይምስም የለሽየተሰኘ ትርጉም ልቦለድ አንብቤ ጨረስኩ::

ትናንትና አርብ ለት ፒያሳ ከሚገኘው British Council ቤተ መፅሃፍት ሂጄ ነበር:: እንደ ጊዜ ማሳለፌያ ነበር የሄድኩት:: አሀ! አዎ ስለ Bronchitis ለማንበብም ፈልጌ ነበር:: አንዲት በቅርብ የማውቃት የናቴ ጉዋደኛ የሆነች ሴት በቅርቡ ሀኪም ቤት ሄዳ ሀኪም “Bronchitis” አለብሽ አላት:: በጣም ያስላታል:: አክታም በብዛት ትተፋለች:: ከዚህ በመነሳት ለምን ስለዚህች ሴት በሽታ አላነብም የሚል ሃሳብ መጣልኝ:: ስለዚህም British Council ተገኘሁ::

 ቤተ መፅሃፍቱ ውስጥ Medicine የሚል ሼልፍ አለ:: እዚያ ሄድኩና የተደረደሩትን መፅሃፍት ሁሉ ቃኘሁዋቸው::  “Pharmacology: Pediatrics: Surgery: Nursing ወዘተ... ለተወሰኑ ደቂቃዎች ካማተርኩ በሁዋላ “Disorders of the Chest” የሚል መፅሐፍ አይቼ አነሳሁት:: አነበብኩ ስለ “Acute Bronchitis” “Chronic Bronchitis” .... “disease of the alveoli” ላል::በተወሰነ መልኩ ማንበቤ ደስ ቢለኝም አሁን ይሕን ማንበቤ ምንም ትርጉም እንደሌለው ሆኖ ተሰማኝ:: ገና ፍሬሽ ማን መጨረሴ ነው:: እንደዚህ አይነቶቹም መፅሃፍት አንብቦ ተረድቶ ለመጠቀም ቢያንስ አራተኛ ዓመት ተማሪ መሆን ያለብኝ ይመስለኛል:: አራተኛ ዓመት ከመደረሱ በፊት ደግሞ ከፊቴ የተደቀኑ ሁለት እንደተራራ የገዘፉ አመቶች አሉ:: በጅጤሳ Preclinical Years ይባላሉ:: የነዚያ ሰው ይበልኝ.....

No comments:

Post a Comment