Monday, February 23, 2015

ግንቦት 5 1984 አ.ም. ረቡዕ
ከምሽቱ 6 ሰዓት ከ51 ደቂቃ ነው:: የዛሬውን ጥናት አጠናቅቄ ወደ ዶርሜ ልክ አሁን መመለሴ ነው::  እየተረሱ  ከሚያስቸግሩኝ ትምህርቶች ዋነኛ የሆነውን ግን ደግሞ የምወደውን አናቶሚ ትምህርት ሳጠና ነበር የቆየሁት:: አንዳንድ ቆራጥ የመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼን በትጋት ማጥናት በመቀጠላቸው እዚያው ማጥኛው ቦታ ጥያቸው ነው የመጣሁት:: ከውጭ የነጎድጉዋድ ድምፅ ይሰማኛል:: ወራቱ በተለምዶ ደረቅ የሚባለው ግንቦት ቢሆንም ሰሞኑን ግን በጅማ ወፈር ያሉ የዝናም ጠብታዎች እየተስተዋሉ ነው.......

ግንቦት 7 1984 አ.ም.  አርብ: ከምሽቱ 5 ሰዓት ከ 37 ደቂቃ
ዛሬ ደግሞ ምሽቱ ነፋሻ ደረቅና በሙሉ ጨረቃ የተዋበ ነው:: ጨረቃን በረዣዥሞቹ የጅጤሳ ፅድና ዝግባ ዛፎች መካከል ባሉት ቀዳዳዎች አሻግሬ ስመለከታት እጅግ ደምቃና አድማሱ ላይ ለኔ ተብላ እንደተቀመጠች  የመንፈስ ምግብ ሆና ትታየኛለች::  ተስፋን ትለግሰኛለች:: በእውነት ለመናገር ነገን እንዳስብ ታደርገኛለች:: ነገን ሳስብም ጎኔን ባልጋ ራሴንም በመከዳ ላይ አሳርፌ አሸልባለሁ..........


በዚህ የትምህርት ሳምንቱ መጠናቀቂያ በሆነ እለት ምሽት ላይ የተሰማኝ አንድ ትልቅ ነገር ቢኖር ፒሲዋንን ገና በሚገባ ያልተገነዘብኩት እንዲሁም ውሉን ያልጨበጥኩት መሆኑን ነው:: መደረግ ያለባቸው ነገሮች እንዲሁም መነበብ ያለባቸው እውቀቶች በፍጥነት ተከማቹ:: ፋታ ጠፋ:: በድንገት ኑሮአችን እጅግ አጭር በሆነ የእንቅልፍ ሰዓት ለሁለት የተገመሰ የሩጫ ዑደት ሆነ:: በዙሪያዬ የማየው ሁሉ እሳት የተነሳ ይመስስል ወደተለያየ አቅጣጫ ይሮጣል:: በዚህ ሁሉ መሃል ግን ማጥናቴን ቀጥያለሁ:: ያነበብኩትን መርሳቴም አብሮኝ:: በየቀኑ ትከሻዬ አካባቢ ውጥረት ይሰማኛል:: የጭንቀት ምልክት ይሆን? በሳምንቱ ውስጥ ባንዱ ወይም በሁለቱ ቀን ምክንያቱ የማይታወቅ የማጥናት አለመፈለግ ስሜት ውስጥ እገባለሁ:: ቢሆንም እንደምንም ወደ ማንበብ መፈለግ አመጣውና በጥናቴ እቀጥላለሁ:: ሌላ አማራጭ የለኝም::ምክንያቱም ከላይ እንዳልኩት በዙሪያዬ የማየው የሚሮጥና የሚተጋ ብቻ ነው:: ለአፍታ ቀጥ ካልኩ ወደሁዋላ መቅረቴና መቀደሜ ነው! ግን ማነው የሚቀድመኝ? በምንስ ነው የቀደመው? በእውነቱ መልሱን አላውቀውም:: በአንድ ዓመት የሚበልጡን የ ፒሲቱ (PC-2) ተማሪዎች ፕሲዋንን አካብደውና እንድንሸማቀቅ አርገው  ስለነገሩን ይሆን እንዲህ የማስበው? በበኩሌ ያው ከሩጫው: ከመፃፉ ብዛትና ከመረሳቱ በተቀር ምንም የሚያስደንቅ ነገር እስካሁን አላየሁም....

No comments:

Post a Comment