Sunday, October 11, 2015

ማክሰኞ ታህሳስ 13 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 6 ሰዓት ከሩብ

የፒሲዋን ትምህርት ጥር 8 ቀን  1985 አ.ም. እንደሚጠናቀቅ ተነግሮናል:: ከዚያ በሁዋላ የማጠቃለያ የፅሁፍ ብሎም የቃል ፈተና ይኖረናል:: የቃል ፈተናውን የሚሰጡን ከሌላ የህክምና ትምህርት ቤቶች የመጡ መምህራን ይሆናሉ.....

ዛሬ ከሰአት በአናቶሚ ላቦራቶሪ ውስጥ የነበረንን ቆይታ በዚህ ማስታወሻ እንድከትብ የገፋፋችኝ ፅጌረዳ እንደሆነች ልብ በል/ይ:: ፅጌረዳ አብረውን ከሚማሩት ሶስት የክምና ተማሪ ሴቶች መካካል አንዷ ስትሆን ማስታወሻ እንደምፅፍ ታውቃለች::

ዛሬ ከሰዓት ፕሮፌሰር ሳላህ ከመጨረሻዎቹ አንዱ የሆነውን የአናቶሚ ላቦራቶሪ ክፍለ ጊዜ በሚደንቅ ሁኔታ አካሄደ:: ይህን ሁኔታ መቸም አልረሳውም:: ፕሮፌሰር ሳላህ ከካዳቨሮቹ ራሶች ውስጥ አንጎሎቻቸውን ፈልቅቆ እያወጣ አሳየን:: እሱ አንድ ከፍ ያለ ቦታ ላይ ቆሞ እኛ ተማሪዎቹ መሬት ላይ ቆመን ክብ ሰርተን ወደላይ በተመስጦ እያየነው አንድ የተገመሰ አንጎል በአንድ እጁ ይዞ በሌላው እጁ ደግሞ በአንጎሉ የውስጥ ክፍል በኩል (medial aspect) እየጠቆመ ብሎም በጎላ ድምፅ በርካታ ስሞችን ነገረን:: ከያንዳንዱም ስያሜ በስተጀርባ ያለውን አገልግሎት ባጭር ባጭሩ አስረዳን.....Internal capsule, putamen, caudate-nucleaus, insula, pallidum, thalamus, ventricles etc.

አሁን ይህን በምፅፍበት ሰዓት ያለሁት በዶርም ቁጥር 207 ነው:: የዶርሙ አባላት በተለያየ ሁኔታና ደረጃ ላይ ይገኛሉ....ማለቴ ጥናትን በተመለከተ ማለት ነው:: አመንቴ የሚባለው ጉዋደኛችን ገና ከእንቅልፉ ተነስቶ አያሌውንና ሚልዮንን እየቀሰቀሳቸው አየሁት:: እነዚህ ሶስቱ እንግዲህ ቀሪውን ሌሊት እስከቻሉና አቅማቸው እስከፈቀደ በንባብና በጥናት ትጋት ለማሳለፍ የሚሹ ናቸው::  እኔ ደሞ ለመተኛት እየተዘጋጀሁ ነው:: ቀስቃሹ ራሱ ግን እንቅልፉን ገና አለመጨረሱ በጉልህ ያስታውቃል:: መልካም ዕድል ተመኘሁለት በልቤ:: አያሌው ላለመነሳት ጥቂት ካንገራገረ በሁዋላ ተነስቶ ፊቱን መታጠብ ጀምሩዋል:: አዳሙ የተባለው ሌላው ወንድማችን  ያለማንም ቀስቃሽ ራሱ ከእንቅልፉ ተነስቶ ማንበብ ለመጀመር እየተሟሟቀ ነው:: አምሳሉ የቤተማርያም አልጋ ላይ ተጋድሞ ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ነው:: ታድሎ! ቤተማርያም በዶርሙ ውስጥ የለም:: ጥናት አምባ ርቆ ተሰማርቷል.......

No comments:

Post a Comment