Monday, October 26, 2015

ጥር ሁለት ቀን 1985 .. ከቀኑ ሰባት ሰዓት
ዉቦቹና በጨረቃ ይደምቁ የነበሩት ምርጦቹ የበጋ ወራት ሕዳርና ታህሳስ ፒሲዋን ማጠቃለያ ፈተና መምጣት ስጋት ተጀቡነው ተራ በተራ በማለፍ ስፍራቸውን ለጥር ለቀቁ:: ጥር ወር ደግሞ  የያንዳችዳችን በጅጤሳ መዝለቅና አለመዝለቅ የሚወሰንበት ወር ለመሆን ታደለ:: ብርቱ የሂወት ፈተና ወቅት:: የድብልቅልቅ ስሜት ወቅት:: ባንድ በኩል አድካሚዎቹ የሌክቸር ክፍለ ጊዜያት የሚያበቁ በመሆናቸው አንፃራዊ እፎይታ ተሰምቶኛል:: በሌላ በኩል ደግሞ ለፈተናው ያደረኩትና ገና የማደርገው ዝግጅት መቼም ቢሆን እንደማይበቃ ከማወቅ የመነጨ የውስጤ መብሰክሰክ ከቀን ወደቀን እየጨመረ ነው:: እነዚህን የጠቀስኩዋቸውን ስሜቶች ሌሎች ሰላሳ ምናምን የሚሆኑ ፒስዋነኞች  እንደሚጋሩኝ እርግጠኛ ነኝ::

የመጨረሻው የፒሲዋን ሌክቸር ቀን በሚቀጥለው ሮብ እንደሚሆን ተነግሮናል:: ከዚያም ሁለት ሳምንት ከጥናትና በጄም ካለ ከክለሳ መሳ ለመሳ የምንገጥምበት ግዜ ይሆናል:: ያም ሲያበቃ  የዓመቱ ማጠቃለያ የፅሁፍ ፈተና በአናቶሚ ትምህርት ይጀመራል:: እንግዲህ ባወጣ ያውጣው......... እኔ ግን ምንም አልተዘጋጀሁምም ከዚህ በሁዋላም የምዘጋጅ አይመስለኝም.....

በነገራችን ላይ ባለፈው ሰሞን ፊዚዮሎጂ ሌክቸር ላይ ስለ Color Blindness ተማርን:: የፊዚዮሎጂ መምህሩ ለናሙና ይዞ የመጣው  Color Blindness መለያ ወረቀት ላይ የተሳሉ በነጠብጣብ የተሞሉ ክበቦች ለምሳሌነት አንዳንድ ተማሪዎችን እየጠራ ስንት ቁጥር ወይም ምን ይታያቹሃል እያለ ሲጠይቅ ከተጠያቂዎቹ አንዱ እኔ ነበርኩ:: ታዲያ እኔ ላይ ሲደርስ ሌላው ሁሉ ስምንት ይሁን አራት ቁጥር ያለውን እኔ ሶስት ቁጥር ነው ብዬ ድርቅ በማለቴ ለመጀመሪያ ግዜ Color Blind እንደሆንኩ ታወቀ:: ቀይና አረንጉዋዴ ቀለሞች አልፎ አልፎ እንደሚምታቱብኝ ቀደም ብዬ የተረዳሁ ቢሆንም አሁን በደንብ ተነቃብኝ....ወይኔ

ጥር 18 ቀን 1985 .. ከምሽቱ 2 ሰዓት  21 ደቂቃ
በእውነቱ የባለፈውን ማስታወሻ ካሰፈርኩበት ከጥር ሁለት ጀምሮ እስከዛሬ ድረስ ባሳለፍኩዋቸው ቀናት የተከናወኑ ድርጊቶች ቢኖሩም ቀናቱ ለኔ ብቻ ሳይሆን ለመላው ፒሲዋነኞች እጅግ አስጨናቂ እንዲሁም የአእምሮን ሉዓላዊነት የሚገዳደሩ ቀናት ስለነበሩ እዚህ ማስታወሻ ላይ አሰፍራቸው ዘንድ ከባድ ሆነብኝ:: እጄም ይፅፍ ዘንድ ሳሳ:: ነገር ግን ይህን እላለሁ: በዚህ ሰዓት የዓመቱ ማጠናቀቂያ የፅሁፍ ፈተና  መጀመሪያ ዋዜማ ላይ ከመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼ ጋር የሞቀ ወሬ ይዘናል:: ጥናት የሚባል ነገር አቁመናል:: ዘራፍም ብለናል:: አልተጨነቅንም ማለት ግን አልነበረም:: ጥቂቶቹ የተናገሩትን እነሆ...
ሚሊዮን "ቀፎኛል"
አምሳሉ "እንግዲህ ጭንቅላቴን የከበደውን አናቶሚ ነገ ልገላገለው ነው: በጣም ራሴን አሞኛል"
መንጌ "ፒሲዋን መርዝ ነው ግን ሰው አይገድልም"
ኃይሉ "ተስፋ ትልቅ ነገር በውስጤ እየኖረ: ሂወት ትንሽ ነገር ታጓጓኝ ጀመረ"


Sunday, October 11, 2015

ማክሰኞ ታህሳስ 13 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 6 ሰዓት ከሩብ

የፒሲዋን ትምህርት ጥር 8 ቀን  1985 አ.ም. እንደሚጠናቀቅ ተነግሮናል:: ከዚያ በሁዋላ የማጠቃለያ የፅሁፍ ብሎም የቃል ፈተና ይኖረናል:: የቃል ፈተናውን የሚሰጡን ከሌላ የህክምና ትምህርት ቤቶች የመጡ መምህራን ይሆናሉ.....

ዛሬ ከሰአት በአናቶሚ ላቦራቶሪ ውስጥ የነበረንን ቆይታ በዚህ ማስታወሻ እንድከትብ የገፋፋችኝ ፅጌረዳ እንደሆነች ልብ በል/ይ:: ፅጌረዳ አብረውን ከሚማሩት ሶስት የክምና ተማሪ ሴቶች መካካል አንዷ ስትሆን ማስታወሻ እንደምፅፍ ታውቃለች::

ዛሬ ከሰዓት ፕሮፌሰር ሳላህ ከመጨረሻዎቹ አንዱ የሆነውን የአናቶሚ ላቦራቶሪ ክፍለ ጊዜ በሚደንቅ ሁኔታ አካሄደ:: ይህን ሁኔታ መቸም አልረሳውም:: ፕሮፌሰር ሳላህ ከካዳቨሮቹ ራሶች ውስጥ አንጎሎቻቸውን ፈልቅቆ እያወጣ አሳየን:: እሱ አንድ ከፍ ያለ ቦታ ላይ ቆሞ እኛ ተማሪዎቹ መሬት ላይ ቆመን ክብ ሰርተን ወደላይ በተመስጦ እያየነው አንድ የተገመሰ አንጎል በአንድ እጁ ይዞ በሌላው እጁ ደግሞ በአንጎሉ የውስጥ ክፍል በኩል (medial aspect) እየጠቆመ ብሎም በጎላ ድምፅ በርካታ ስሞችን ነገረን:: ከያንዳንዱም ስያሜ በስተጀርባ ያለውን አገልግሎት ባጭር ባጭሩ አስረዳን.....Internal capsule, putamen, caudate-nucleaus, insula, pallidum, thalamus, ventricles etc.

አሁን ይህን በምፅፍበት ሰዓት ያለሁት በዶርም ቁጥር 207 ነው:: የዶርሙ አባላት በተለያየ ሁኔታና ደረጃ ላይ ይገኛሉ....ማለቴ ጥናትን በተመለከተ ማለት ነው:: አመንቴ የሚባለው ጉዋደኛችን ገና ከእንቅልፉ ተነስቶ አያሌውንና ሚልዮንን እየቀሰቀሳቸው አየሁት:: እነዚህ ሶስቱ እንግዲህ ቀሪውን ሌሊት እስከቻሉና አቅማቸው እስከፈቀደ በንባብና በጥናት ትጋት ለማሳለፍ የሚሹ ናቸው::  እኔ ደሞ ለመተኛት እየተዘጋጀሁ ነው:: ቀስቃሹ ራሱ ግን እንቅልፉን ገና አለመጨረሱ በጉልህ ያስታውቃል:: መልካም ዕድል ተመኘሁለት በልቤ:: አያሌው ላለመነሳት ጥቂት ካንገራገረ በሁዋላ ተነስቶ ፊቱን መታጠብ ጀምሩዋል:: አዳሙ የተባለው ሌላው ወንድማችን  ያለማንም ቀስቃሽ ራሱ ከእንቅልፉ ተነስቶ ማንበብ ለመጀመር እየተሟሟቀ ነው:: አምሳሉ የቤተማርያም አልጋ ላይ ተጋድሞ ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ነው:: ታድሎ! ቤተማርያም በዶርሙ ውስጥ የለም:: ጥናት አምባ ርቆ ተሰማርቷል.......

Sunday, October 4, 2015

አርብ ታህሳስ 2 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 6 ሰዓት

ፒሲዋን የተሰኘው የጅጤሳው ሕክምና ትምህርት ዓመት (ክፍለ ዘመን ብለው ይቀለኛል) ሊጠናቀቅ የቀሩት 5 ሳምንታት ወይም ሰላሳ አምስት ቀናት ብቻ ናቸው:: ይህን ሀቅ ዛሬ በመረዳቴ ከእንቅልፌ ቀስቅሰው “ስማ አንድ ሳምንት ብቻ ቀረ!!!” ያሉኝ ይመስል ክው ብዬ ቀረሁ:: ላለፈው ዓመት ያህል የትምህርት ግዜ በየቀኑ የተለፈለፉ እውቀቶች: ሃሳቦች: መላምቶች: የሰው ልጅ ህልውና ሳይንሶች: አበላሎች: አተነፋፈሶች:  አወላለዶች: አስተሳሰቦች: አጠቃላይ አሰራሮች: ጭንቅላቴ ውስጥ በተዘበራረቀ ሁኔታ ተከምረውና ተጠቅጥቀው የሚገኙ ሲሆን: የተፃፉ ግን ያልተነበቡ ነጥቦች: ፅሁፎች: የተሳሉ ግን በድጋሚ ያልታዩ የአናቶሚ ስዕሎች እንዲሁም የፊዚዮሎጂ: የባዮኬምስትሪ ግራፎች: አልጎሪዝሞች: ሳይክሎች: ሂደቶች: ፍጭቶች: ግኑኝነቶች: ወዘተ.....በበርካታ ደብተሮችና ማስተወሻዎች  ላይ ሰፍረው: በእኔ በሳምሶን መገለጥን እየጠበቁ በተጠንቀቅ ላይ የሚገኙ መስሎ ይሰማኛል:: ለመጨረሻው የፅሁፍም ሆነ የቃል ፈተና በብቃት እቀርብ ዘንድ ፒስዋንን ሀ ብዬ ከጀመርኩበት ከሚያዝያ ወር 1984 አ.ም. ጀምሮ የተስተማርኩትን: በቅንጭላቴ እንዲሁም በደብተሬ ያኖርኩትን ሁልቆ መሳፍርት እውቀት መልክ መልክ ማስያዝ ይጠበቅብኛል:: በዚህ በጠቀስኩት ግንዛቤ ያለምንም ማጋነን ደንግጫለሁ:: በቀላሉ ሀኪም አይኮንም ለካ.......

እሁድ ታህሳስ 4 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 12  ሰዓት ከ 39 ደቂቃ


በዚህ የአእምሮ ውጥንቅጥ ውስጥ ባለሁበት ወቅት አንድ ቆይቶ በጣም ያሳቀኝን ነገር ከጉዋደኛዬ ከአብይ ጋር ፈፀምኩ:: እሱም እንደኔ በፒስዋን መጨረሻ መድረስ የድንጋጤ መንፈስ ውስጥ ሳይገባ አይቀርም:: ዛሬ ቀን ላይ እኔና አብይ ገላችንን ለመታጠብ እኩል አሰብን:: ተገናኝተን ወደገላ መታጠቢያ ቤቱ እየሄድን ሳለ የመሄዱን ሃሳብ ድንገት በመተው ውሃ በባልዲ ሞልተንና ተሸክመን ወደ ማደሪያ ዶርማችን ተመለስን:: ልብሶቻችንን አወላልቀን የዶርሙ መሃል- ለመሃል- መሃል ላይ በመቆም በባልዲ ጭነን ያመጣነውን ቀዝቃዛ ውሃ ገላችን ላይ እያፈሰስን ታጠብን.....ሳሙና ተለቀለቅን: እንደገናም ገላዎቻችን ላይ ውሃ ቸለስን:: ማደሪያ ዶርማችን ውስጥ ማለት ነው:: ሌሎቹ የዶርም ተጋሪዎቻችን ባካባቢው አልነበሩም:: ዶርም ውስጥ ገላችንን ለመታጠብ ያነሳሳንን ምክንያት በትክክል ባላስታውሰውም ና አብይ የሚሰማውን ባላውቅም ያደረግነውን ነገር ለብቻዬ በተደጋጋግሚ እያሰብኩ ከመሳቄ የተነሳ ጭንቀቴ ቀለል እንዳለልኝ ግን እርግጠኛ ነኝ........