Wednesday, February 5, 2014

ምቾት አልባ ጅምር

ጥቅምት ፩፰ ፩፱፰፫ አ.ም.

ምቾት አልባ ጅምር...

ዛሬ ጅማ ከደረስኩ ልክ አንድ ወር ሆነኝ:: የቤተሰብና የሰፈር ናፍቆት እየለቀቀኝ የሄደ ቢሆንም የቀዩ ሸክላ አዳራሽ ኑሮ ግን በጭራሽ አልተስማማኝም:: በተደጋጋሚ የሐይ ስኩል ተማሪነት ግዜዬ ና ትምህርት ቤቴ ራሱ እንዲሁም ያለፈው ዓመት ወራቶች በመልካም ሁኔታ ትዝ ይሉኛል:: ፀጥታን ከምንም በላይ የምወድ መሆኔን ያወቅሁት እዚህ አዳራሽ ውስጥ ነው:: መኖሪያ ቤታችን በስተጉዋሮ ከመሬት አንድ ሜትር ከፍ ብላ የምትገኘው የመኝታ ና የ ጥናት ከፍሌን አስታወስኩ:: ሃይ ስኩልን ሙሉ የሄድኩበት አዲስ ከተማ ትምህርት ቤት የጠዋት ክፍለ ግዜ ሲጠናቀቅ አልፎ አልፎ መፅሐፍት ቤት ለመሄድ ካልሆነ በቀር ዘወትር ወደ ቤት ነበር የምገሰግሰው:: ታዲያ ከሰዓት በሁዋላ ሰፈራችን ፀጥ ይላል:: በፀሃያማዎቹ  የበጋ ወራት ከቀትር በስቲያ አልፎም በከዋክብት ና በጨረቃ ደምቆ ፀጥታን በተላበሰ ሌሊት ደብተሮችና ና መፅሐፍት ገላልጬ ከጥናት ጠረጴዛዬ ላይ የማሳልፈው ግዜ ታወሰኝ:: አንዳንዴ ከ አሮጌው ቴፕ ረኮርደር የሚወጡ የአማርኛ ዘፈኖችን እየሰማሁ ከ College Physics/Algebra መፅሀፎች የ ፊዚክስ ና የሂሳብ ጥያቄዎችን ስሰራ የሚነጋበት አጋጣሚ አለ:: ያ... ለብቻዬ ነገሮችን አከናውንበት የነበረውን ግዜ አሁን እዚህ ላገኘው አልቻልኩም:: እስቲ አንቺ ማስታወሻዬ አስቢው አንድ ሰው ከ ጥቂት ወራት በፊት ለብቻ ግዜን ከማሳለፍ ተነስቶ በድንገት ከ ፬፱ ሌሎች ሰዎች ጋር በ አንድ ጣራ ስር ሲያድር እንዴት አዲስ አይሆንበት?:: ጩሀት: ወሬና ገርግር ቀኑን ሙሉ የአዳራሹ መለያ ምልክቶች መሆናቸውን ቀጥለዋል:: 

ሌላው የሚገርመው እዚህ አዳራሽ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ምንም ጉልበት የሚጠይቅ ሥራ ሳልሰራ ድካምን መቀዳጀቴ ነው:: ኮሌጅ ውስጥ እንደዚህ አይነት ስሜት መቼም አስጊ ነው: ምክንያቱም በድካም ጥናት አጠና መፅሀፍም አንብቤ እረዳ ዘንድ ከቶ አይቻለኝም:: ምሽት ላይ እንደሌሎቹ እኔን መሰሎች ቀን ትምህርት በምንቅስምበት ሌክቸር አዳራሽ ተገኝቼ ለማንበብ: ከንባቡ ውስጥም ፍሬ ነገሩን እየቁዋጨሁ ወደ ትውስታ ማህደር ለማኖር ስሞክር በመጀመሪያ አይኖቼ በእንባ ይሞላሉ: እንደ አለርጂክ መሆኑ ነው:: ያሳክከኛል ሁሉ:: ከዚያም ቶሎ ቶሎ በረጅሙ ያዛጋኛል ብሎም አልጋ ላይ ስወጣ ብቻ የሚጠፋው እንቅልፌ ይመጣል:: እሺ ይበቃኛል ብዬ ና ትቸው ወደ ቀዩ የሸክላ አዳራሽ እንዳልመለስ ከጥናት ና ቀን ከሞነጫጨሩት ማስታወሻ ጋር ጉሮሮ ለጉሮሮ ተናንቀው ያቀረቀሩት ሌሎቹ እኔን መሰሎች ያስቀኑኛል::  ማስቀናት ብቻ አይደለም ውስጣዊ ሽብር ይነዙብኛል....

ለመጀመሪያ ግዜ ከዚህ ትምህርት ቤት ወድቄ እባረር ይሆን? ብዬ አሰብኩ:: የ ክሪስማስን ፈተና በርቀት አስቤው የማልፈው አልመስልህ አለኝ:: ለዚህ አይነት ስሜት በውስጤ መፈጠር ምክንያት ከሆኑት ክስተቶች አንዱ በቀደም ለት የተሰጠን የባዮሎጂ ና የ ኬሚስትሪ ላቦራቶሪ ረፖርት ውጤት ነው:: ባዮሎጂ ስምንት ከ አስር እንዲሁም ኬምስትሪ ሰባት ከአስር ይላል የኔ ውጤት:: ጅጤሳ ትመህርት ከጀመርኩ የመጀመሪያዎቹ የሆኑት እነዚህ ውጤቶች አላስደሰቱኝም:: ወይኔ ሃይ ስኩል! ይባስ ብሎ የከሚስትሪ ውጤት ላይ "Please do not copy from your friend" የሚል አስተያየት ተፅፎበታል:: ወይ አምላኬ.........


No comments:

Post a Comment