Tuesday, August 25, 2015

ጨረቃ
ወኔዬ አልቆ ተሙዋጦ 
መንፈሴም ደክሞ ተስፋ ቆርጦ
ብስጭት ገብቶኝ ሞትን ስሻ
መሄጃ አጥቼ መድረሻ
ወደበላዬ ስመለከት
ሰማይ ከዋክብት ወዳሉበት
አየሁ ጨረቃ መሃል ሆና 
ምድርን ስታደምቅ በብርሃኗ
እነሆም ተስፋዬ አንሰራራ
ልቤ ተነካ ባምላክ ስራ 
ብቻዬን እዳልሆንኩ ተገነዘብኩ
ነገን እያሰብኩ አሸለብኩ
(By Samson Haile)

ማክሰኞ መስከረም 19 ቀን 1985 አ.ም.  ከምሽቱ 6 ሰኣት ከ 13 ደቂቃ

ዛሬ ጠዋት ፊዚዮሎጂ ሌክቸር ከመውሰዳችን ቀደም ብሎ ፕሮፈሰር ማሂን ከግንዛቤ በማስገባት አንደሚጨንቀኝ አስቤ ነበር:: ግን ሳልጨነቅ ቀረሁና ያ ደግሞ አስጨነቀኝ:: እንዴት ሳይጨንቀኝ ቀረ? 
ለነገሩ ለማን ብዬ ነው የምጨነቀው? አንድ አስተማሪ ደበረኝና ምን ይጠበስ? 

በነገራችን ላይ ፒሲ ዋን ሁለተኛ ሴሚስተር በደንብ ተጀመረ:: ዛሬ አስከ ምሽቱ ሰባት ሰአት ለማንበብ እቅድ የነበረኝ ቢሆንም አሁን ደከመኝ: 47 ደቂቃ ሲቀር ማለት ነው.....

ውድ ማስታወሻዬ እኔ ካሁን ወዲያ ላንቺ የምነግርሽ የጨረቃን ድምቀት: የጸሃይን ጥልቀት: የዛፎችን ውዝዋዜና የነፋስን ሽውታ ነው እንጂ በቃ ጭንቀት አላወራም:: ኦ ጭንቀት ልኩ እንዴ? አላወራም ብዬ ስለሱ....

የግቢው አትክልተኛ አበቦቹን በደንብ እያሳመራቸው መሆኑን ተመለከትኩና  አንድ ላንቺ ማለት ያለብኝ ነገር ትዝ አለኝ:: "ጥሩ ቀለማትን ከማየት የበለጠ ምን ነገር አለ?" እላለሁ አንዳንዴ:: በእርግጥ በሙዚቃና በስነጽሁፍ ብደሰትም የሰዎች ስራ ከሆኑት ከነዚህ ይልቅ በተፈጥሮ ህብረ ቀለማት ና የወፎች ዝማሬ ይበልጥ የመደሰት ባኅሪ ያለኝ ይመስለኛል......

ሮብ መስከረም 20 ቀን 1985 አ.ም.
ዛሬ ማታ ከቤተመሃፍት ንባብ ለምስት ደቂቃ እረፍት ለማድረግ ወጥቼ ሳለ የኢንተርንሺፕ ሃኪም የሆነው አብርሃም ሻይ ገዛልኝና ከዚያ በሁዋላ ደስ እያለኝ ጠናሁ:: ቤተመጽሃፍቱ ሲዘጋ እንደተለመደው ወደ ሌክቸር ሆል ሄድኩ:: ወደዚያ እየሄድኩ ወደ ሰማይ ቀና ብዬ አየሁ:: ግማሽ ጨረቃ ትታያለች:: ልቤን በእርግጥ ደስ እንዳለው ይታወቀኝ ነበር:: ከዚህ በሁዋላ በሌክቸር ሆል ውስጥ በንባብ እስከ ምሽቱ 6 ሰኣት ከ40 ደቂቃ ቆይቼ ለመተኛት ወደ ዶርም ኣቀናሁ:: በመንገዴ ላይ እመቤት አብራኝ ነበረች:: ዝናብ እያካፋ የነበር ቢሆንም ርምጃችን የወትሮው ነበር.....

ሐሙስ መስከረም 28 ቀን1985 አ.ም. ከምሽቱ 7ሰኣት ከ 13 ደቂቃ
ዛሬ እንኩዋን የማወራው ነገር የለኝም:: ግን ጨረቃ በሙሉ ድምቀት በሰማያዊ ሰማይ ላይ እየታየች መሆኑን ሳልገልጽ መተኛት ከበደኝ:: ዶርም ቁጥር 207 ውስጥ አልጋዬ ላይ ነኝ:: የምጽፈው ማጣቴን ላልተኙ ጉዋደኞቼ እየነገርኩዋቸው ነው:: መንጌ ልጋው ውስጥ የገባ ቢሆንም አልተኛም:: የሆነ ነገር ይዞ ያነባል:: አባይም እንደዚያው:: አብይ ትንሹዋ ጠረጴዛ አጠገብ ሆኖ እያጠና ነው:: አሌክሱ አምሳሉ ሚሊዮንና ሃይሉ እንዲሁም ቤተማርያም እርግጡን ለመናገር ባልችልም እንቅልፍ ውስጥ ይመስሉኛል:: አባይነህ፥ አመንቴ ና አዳሙ የሉም:: ገና ኣልገቡም:: ውድ ማስታወሻዬ ደህና እደሪ:: ጉዋደኞቼም እንዲህ ይሉሻል.....

ባይ "እግዚኣብሄር ይመስገን"
መንጌ " God should be praised"
አብይ "ኑሮ መሮኛል"

No comments:

Post a Comment