Tuesday, March 14, 2017


መስከረም 12 1988 አ.ም.

ዛሬ በተማሪዎች ቴሌቪዥን መመልከቻ አዳራሽ ውስጥ “No Place to Hide” የተሰኘው ፊልም ሲታይ እኔም ታደምኩ:: እጅግ የወደድኩት ፊልም ነው:: በልቤ ውስጥ ካለው ነገር ጋ የሚሄድ ጠንካራ ትርጉም አገኘሁበት:: በፊልሙ ውስጥ ያለው ዋና ገፀ ባህሪ በኔ ሚዛን እጅግ መልካም እንዲሁም እውነተኛ: እውነትን ለመታደግ ብሎም ሕግን ለማስከበር የቆመ ስለነበር ወደድኩት::



መስከረም 13 1988 አ.ም. - ራሴን ሳክም

አልፎ አልፎ እንደሚያደርገኝ ዛሬ ደብሮኝ ነበር:: ቀላል ድብርት አይደለም:: ትልቅ የሆነ ድብርት ከነጉዋዙ:: የመሰላቸት ስሜት የገነነበትና በራስ የመተማመን ስሜት ጥቂት የሆነበት:: “የፍልስፍና ሙድ” ውስጥ ነበርኩ:: አለማችን እግዚአብሔር ቆንጆ አድርጎ ቢፈጥራትም በዘመንና በሰው ልጆች ትብብር ቆሽሻ ታየችኝ:: የራሴን ምንነትና በዚህ የቆሸሸ ዓለም ላይ ያለኝን ቦታ ለራሴ ጠየቅሁ:: ራሴን የሆነ ቦታ መመደብ ፈለግሁ ግን ቦታ አጣሁ:: ያለማቁዋረጥ እንቶፈንቶ አሰብኩ:: ለቅፅበት ፍርሃት ውስጥ ገባሁና ወጣሁ:: የያዝኩት ሕክምና ትምህርት ዳግም ከመቸውም የበለጠ ከብዶ ታየኝ:: ተስፋ መቁረጥ ጀምሬ ተስፋ መቁረጤ ራሱ አስፈራኝና ተውኩት::በመፅሐፍ ቅዱስና በታገል ሰይፉ ግጥም ላይ ያነበኩትን የእምባቆምን ለቅሶ አስታውስኩ:: በእግዚአብሔር ታላቅ ተስፋን ለማድረግ ወሰንኩና መተንፈስ ቀጠልኩ........



መስከረም 14 ና 15 1988 አ.ም. - ቻዎ ሰርጀሪ

ዙሩን ለመጨረስ ሶስት ሳምንት ሲቀረኝ ቀዶ ጥገና (surgey) ትምህርት በማያሻማ ሁኔታ ሰለቸኝ:: በቃ በግልፅ ለመናገር  ከዚህ በሁዋላ የተንዛዛ (ቦሪንግ) ነው:: ይህ አምና ስፔሻላይዝ አደርግበታለሁ እንዲሁም በቀዳሚነት እወደዋለሁ ያልኩት ፊልድ የኔ እንዳይደለ ጥርት ብሎ ታየኝ....ቻዎ



መስከረም 17 1988 አ.ም. ሐሙስ ጠዋት - መስቀል

ከዛሬው ይልቅ ስለትናንት ማታ ልናገር:: ለኔና ለጉዋደኞቼ ጥሩ ምሽት ነበር:: እኔና እነመንጌ የመስቀል ዋዜማ በመሆኑ እንደተለመደው: ምሽቱን ወጣ ብለን ለማሰለፍ ሳንቲም አሰባሰብን:: ሳንቲም ካላቸው ጉዋደኞቻችን ተበደርን: አሮጌ ልብሶችና ጫማዎች ገበያ ወደን ጆሮ ግንዳቸውን አልን: ከዚያም ወደ ጅማ ከተማ እምብርት ሄድን...ጠለቅን:: በቅርብ የተዋወቁት መሃንዲሱ ጉዋደኛዬ ጌታሁን አብሮን ስለነበር የኔ ደስታ እጥፍ ነበር:: ሌላው ምሽቱን ልዩ ያደረገው ግርማ ሁንዴ ለመጀመሪያ ግዜ ምሽት ላይ እኛን መቀላቀሉ ነው:: እርሱ ደሞ ቀን ላይ አዲስ መጫሚያ ገዝቶ ስለነበር ተመችቶት ነበር:: ብዙ ግዜ እንዳደረግነው ወይን ጠጅ እየጠጣን ደነስን:: ዶርማችን ስንመለስ መንግስቱ ከሌሎቻችን በገዘፈ ሞቅታ ተኝተው የነበሩትን ጉዋደኞቻችንን ቀሰቀሳቸው:: ነገርግን እነሱ መንም ቅር አልተሰኙበትም:: ምክንያቱም መስቀል በተለምዶ የጉራጌ በዓል ነው ስለሚባል .............

No comments:

Post a Comment