Wednesday, March 5, 2014

ወደ ብላቴ ስንሄድ - ክፍል አንድ

መጋቢት ፩፬ ፩፱፰፫ አ.ም.

ያ ዶሮዬ ጮከ መንጋቱን ነገረኝ 
በዛሬው ቀን ላርደው ቀጠሮ ነበረኝ 
(ታገል ሰይፉ)

የጅማ አየር ከወትሮው በባሰ ሁኔታ ሞቅና ከበድ አለ:: በሰማዩ ላይ የተንጣለሉት ደመኖች ሊወድቁ የደረሱ መሰለ:: በዚህ እኔና ጉዋደኞቼ ነገሮችን ጠለቅ ብለን በማናስብበት: ፖለቲካም በማይገባን ጨቅላ እድሜ ሳይታሰብ የከፋ ግዜ ብቅ አለ:: ሊቀመንበር መንግስቱ "ዘራፍ!"ብለዋል ተባለ:: ሰኞ: ማለትም ከሁለት ቀናት በሁዋላ የጤና ሳይንሱ ተማሪዎች በሙሉ ወደ ውትድርና ማሰልጠኛ ጉዞ በመጀመር መላውን የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ ና ኮሌጅ ተማሪ ዘማቾች እንዲቀላቀሉ የተወሰነ መሆኑ ሲነገር ተማሪ ሁሉ የድንጋጤ ድባብ ተላበሰ:: ከጥቂት ቀናት በፊት በቴሌቪዥን ያየነው የጋለ ና በፍላጎት የተደረገ የሚመስለው የአዲስአበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በሊቀመንበር መንግስቱ ፊት ያሰሙት ጩሀት ቅርፁን ቀይሮና ፈጣን ትእዛዝ ሆኖ ወደ ጅጤሳ መጣ:: ትእዛዙን ተከትሎ የአብዛኛው ተማሪ ባህሪ ለውጥ አሳየ:: ሳቅ የሚባል ነገር ጠፋ:: ጭምት: ዝምተኛና ከስታራ በዛ:: መራወጥና መተራመስ ተጀመረ.....

ዛሬ ከሰዓት የአራተኛ ዓመት ሕክምና ተማሪ ከሆነው የሰፈሬ ልጅ ታጠቅ ጋ በመሆን አልፎ አልፎ እየሄድን ወደየቤታችን ስልክ ከምንመታበት የጅማ ቴሌ (ስልክ ቤት) ሂጄ ነበር:: እንደጠበኩት ስልክ ቤቱ  በተማሪዎች ተጨናንቆ ነበር :: "ጉዞ ጀምሩ ተብሉዋል" "ጉዞ መጀመራችን ነው" የሚሉ መልክቶች ከጠባቦቹ ና አንድ ውይም ሁለት ሰው ብቻ ከሚይዙት የስልክ መደወያ ክፍሎች ውስጥ በተደጋጋሚ ሰማሁ:: አንዳንዱ ተማሪ ከድንጋጤና ከመረበሽ የተነሳ ነገሮችና አካባቢውን ማስተዋል ተስኖታል:: አንድ ተማሪ ተራውን ጠብቆ አንድ ግዜ በተመታለት ስልክ አናግሮ ከጨረሰ በሁዋላ ከመነጋገርያው ጠባብ ከፍል ውስጥ አንገቱን አስግጎ ኦፕሬተሯን "እባክሽ እንደገና ደግሞ እገሌ ጋ ደውይልኝ" አለ:: ሐምሳ የሚሆኑ ሰልፍ ይዘው ተራቸውን የሚጠብቁ ሌሎች ተማሪዎች ባንድነት ስለጮሁበት የውር ድንብሩን እየሮጠ ከቴሌው ወጣ:: እኔ በሩ ላይ ስለነበርኩ ባይኔ ተከተልኩት: ከወጣም በሁዋላ ሩጫውን አላቆመም...እኔ ቤተሰቤን በስልክ እንደማላገኛቸው እርግጠኛ ነበርኩ:: ምክንያቱም በፊት እንኖርበት የነበረውን  ቤት ለቀው ነገ አዲስ ቤት ውስጥ ይገባሉ:: ስለዚህም መስመሩ ስለሚቁዋረጥ...ስልኩ አይሰራም የሚል ግምት ነበረኝ:: ቢሆንም ደወልኩ...እንደገመትኩት ነው ስልኩ አይመልስም:: ታጠቅ ደወለ:: እህቱ ነበረች ስልኩን ያነሳችው:: ሁኔታውን ሲገልፅላት ክፉኛ እንደደነገጠች ገምቻለሁ:: ታጠቅ ከእህቱ ጋ ያረገውን ንግግር ጨርሶ ስልኩን ሲዘጋ ፊቱ ላይ ሃዘን ይታይ ነበር:: እህቱ ስታለቅስ እንደነበር ና የሚላትን ልትሰማ እንዳልቻለች እየቀፈፈው ነገረኝ:: 

የአንደኛና የሁለተኛ ዓመት ተማሪዎች በሙሉ ዛሬ የተውሶ መፅፍቶቻቸውን ለትምህርት ቤቱ አስረከቡ:: ነገ ደሞ አልጋና ቁምሳጥን ይመልሳሉ ተብሉዋል:: ብዙ ተማሪዎች ያላቸውን የግል ዕቃ በሙሉ ልክ ለእረፍት ወደ ቤት እንደሚሄድ ሰው በሻንጣ ሲሸክፉ ዋሉ:: ግዙፍ የ ሽብር ና መረበሽ ድባብ ሰፍኑዋል::   

የሬዲዮና የቴሌቪዥን ዜናዎች ሁሉ ስለ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የዘመቻ ጥያቄና ምዝገባ ወሬውን በሰፊው እያናፈሱት ነው:: እዚህ ግን ከተማሪዎች ዘንድ የሚነገር የጥርጣሬ አስተያየት እሰማለሁ:: "እስካሁን ድረስ አንድም የተንቀሳቀሰ ኮሌጅ የለም:: አንዳንድ ተማሪዎች ከየኮሌጁና ዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ እየጠፉ ነው:: የጥቁር አንበሳ ሕክምና ተማሪዎች የዘመቻውን ጥሪ አልተቀበሉትም:: ና ወዘተ... ቅዳሜ ተመዝግበን ሰኞ ለጉዞ መታዘዛችን በሁለት ቀናት ውስጥ ከቤተሰብ ጋር በቂ የሆነ የስልክ ግኑኝነት ለማድረግ የማያስችል በመሆኑ: ተማሪዎች እርስበርሳቸው ከሚነጋገሩት ወሬ ለመገመት እንደቻልኩት ሰኞ የመሄዱን ጉዳይ ማንም የተቀበለው አይመስለኝም: ለማንኛውም ነገ ጠዋት ስብሰባ ያለ ይመስለኛል....

No comments:

Post a Comment