መጋቢት ፩፭ ፩፱፰፫ አ.ም. ስድስት ሰዓት ከ ሃያ ሰባት ደቂቃ
ወደ ብላቴ ስንሄድ ከፍል ፪
"It's been too hard living, I am afraid to die
Cos I don't know what's out there beyond the sky"
From Sam Cooke's song A change is gonna come
ከትናንት ወደዛሬ የተማሪዎች ስሜትና ባጠቃላይ ነገሮች ከረር ና መረር እያሉ የሄዱ መስሎ ተሰምቶኛል:: በየደቂቃውና ሰኮንዱ በተማሪዎች ውስጥ አዳዲስ ጥያቄዎች ይፈጠራሉ:: ዛሬ ጠዋት ለሀገራችን የምንዘምት ከሆነ እኛም የምንጠይቀው ጥያቄ ይሟላልን የሚል አስተያየት ሰማሁ:: ሌሎችም ብዙ አይነት ጥያቄዎቹ እየተንሸራሸሩ ነው:: የ ጅጤሳ ዲን የሆኑት ዶክተር ተክለ ፅዮን የመሩት አጠቃላይ ስብሰባ ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት ጀምሮ በመሰብሰቢያው አዳራሽ ዉስጥ ተደረገ:: በርካታ ጥያቄዎች ከተማሪዎች ወደ ዲኑ ጎረፉ:: የጥያቄዎቹ ይዘት ማሰልጠኛ የምንሄድበት ቀን ይራዘም ከሚለው ለዘብተኛ መሰል አስተያየት ጀምሮ ወደ ማሰልጠኛ ከመሄዳችን በፊት የደርግ ባለስልጣኖች ይውረዱ እስከሚለው ንዴት የተቀላቀለበት ጥያቄ ይደርሳል:: በሕልሜ ነው የመሰለኝ:: ዲኑ አብዛኛውን ጥያቄ አልመለሱትም:: በእርግጥ "በቀጥታ ለበላይ አካል አስተላልፋለሁ" የሚለውን ሐረግ ወደ መቶ ግዜ ደጋግመው ተናግረዋል:: ለማንኛውም በስብሰባው መጨረሻ ላይ በአዳራሹ የተሰበሰቡት የጤና ሳይንሱ ተማሪዎች በሙሉ ባንድነት ባሰሙት ጩሄትና ጭብጨባ የታጀበ አስተያየት በአንድ ነባር ተማሪ ተወረወረ:: "የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የዘመቱ ስለመሆናቸው በቂ ማስረጃ እስካላገኘን ድረስ የትም አንንቀሳቀስም!!" ከ ግማሽ ሰዓት በሁዋላ ማለትም ከቀኑ ሰባት ሰዓት በዚሁ አዳራሽ ውስጥ እንደገና ስብሰባ ይካሄዳል:: ዶክተር ተክለፅዮን ከመንግስት ምክር ቤት ጋ ተነጋግረው የሚሰጡንን ምላሽ ለመስማት ይመስለኛል.....
ከጠዋት ጀምሮ በሰማይ ላይ የተንጣለለው ደመና አልገፈፈም:: እኔን ጨምሮ ብዙ ተማሪዎች ወደየት እንደምንሄድ አንወቅ እንጂ እቃችንን በሻንጣ ሸክፈናል:: አንዳንዱ ተማሪ የተጠቀጠቀ ሻንጣ ይዞ ከ ጤና ሳይንሱ ግቢ ሲወጣ ይታያል:: እንደማስበው ለክፉም ለደጉም ጅማ ያለ ወዳጅ ዘመዱ ጋ ውድ የሚላቸውን እቃዎች ለማኖር ነው:: ከዚህም በላይ ቅድም ስብሰባው ላይ ከጥቂት አልባሳትና ጫሞች በቀር የምትይዙት ዕቃ እንዳይኖር ተብለናል::
በያንዳንዱ ልብ ውስጥ ያለውን መገመት ቢያያዳግተኝም ቢያንስ ሁሉም የማየው ፊት የከፋውና የቀፈፈው መሆኑን ግን እርግጠኛ ነኝ:: እኔ ራሴ ቀፎኛል:: እንደበፊቱ ፈታ ልል አልቻልኩም:: ተማሪዎች በየኮርነሩና ጥጋጥጉ ተሰባስበው የሚያወሩት ስለዘመቻው ብቻ ነው:: በአንዳንዶቹ ስብሰባዎች ላይ እኔም ራሴ እየተካፈልኩ እንደሌሎቹ ሁሉ አስተያየት እሰጣለሁ:: እንደአብዛኛው ተማሪ ሁሉ የዘመቻውን ሃሳብ አልደገፍኩትም....
ከቀኑ ሰባት ሰዓት ደረሰ:: ስብሰባም ተደረገ:: ስለስብሰባው ዝርዝር መግባት ሳያስፈልገኝ ማለት የምችለው ነገር ዶክተር ተክለ ፅዮን እኛን ከዘመቻ ለማስቀረት የሚያስችል ኃይል አልነበራቸውም:: ከመንግስት ምክር ቤት ያመጡት ምንም አይነት ምላሽ አልነበረም:: በቃ በማንኛውም ሁኔታ ወደ ውትድርና ማሰልጠኛ እንድንሄድ ተውስኗል:: የወሰነውን እግዚአብሔር ይይለት! ስብሰባው ያለምንም መደምደሚያ ተበተነ:: አሁን የምሬን ነው: ልቤን የሆነ የተደበላለቀ ስሜት ተሰማው:: ከዚህ በሁዋላ በእርግጥም ውሳኔው የግል እንደሆነ ገባኝ:: የቡድንም ሆነ አጠቃላይ ስብሰባ ዋጋ የለውም:: ምን ባደርግ ይሻለኛል? ምናልባት አብዛኛው ተማሪ ወደሚለው ማድላት ሳይሻለኝ አይቀርም:: ግን ሌላው ተማሪ የወሰነውን እንዴት ማወቅ ይቻላል? ለመወሰን ተቸገርኩ:: ምክንያቱም መሄድም መቅረትም አደገኛ ነው::
በዚሁ ቀን ምሽት ላይ ወደመመገቢያው አዳራሽ ከጉዋደኞቼ ጋር እራት ልንበላ ስንገባ ወጥ ታወጣልኝ የነበረችው ሴት ፊቱዋ ሃዘን የተላበሰ ብቻ ሳይሆን አይኑዋ አብጦ ስታለቅስ የነበረ መሆኑን ይናገራል:: ይህንን ብረዳም ዘወትር ከወጥ ቤቶቹ ጋር እንቀላለድ ስለነበር " እንግዲህ የመሰነባበቻውን ከወጡ በደንብ" አልኩዋት:: "እባክህ ተወኝ" ብላ እምባዋን እንደገና ዘረገፈችው......
‹‹ምንድን ነው መንቅቦቅ! ቦቅቧቃ ሁላ! ጎጃምና ጎንደር ተይዞ እንዝመት፤ አንዝመት ጭቅጭቅ! እንኽድ ካላችሁ እንኽድ፤ አንኸድምም ካላችሁ እንኽድ!›› Late Aklilu Takele
ReplyDelete