Thursday, November 24, 2016

ጳጉሜ 6 ቀን 1987 ሰኞ
ዛሬ 1987 .. የመጨረሻ ቀን ነው: ጳጉሜ 6:: የዶርሚቶሪ አልጋዬ አጠገብ ብቻዬን በትካዜ ተቀምጫለሁ:: በክፍሉ ዉስጥ ከኔ በስተቀር ማንም የለም::: በልቤ ውስጥ ያለን ነገር ለማውጣት እየታገልኩ ነው:: ለምን እንደሆነ ባላውቅም የተለያዩ ሀሳቦች በእንግሊዝኛ አምሮዬ ውስጥ ይመላለሳሉ ግን በጽሁፍ አሳምሬ እንዳላስቀምጣቸው የቁዋንቁው ችሎታ ያጥረኛል:: በክፍሉ መስኮቶች አሻግሬ ስመለከት ዝናብ ሲዘንብ ይታየኛል ድምፁ ግን አይሰማኝም:: ቀፋፊ ቀን:: ምንም የምሰራው ነገር የለም:: የአዲስ አመት ዋዜማ በመሆኑ የትምህርተ-ሂወት እንቅስቃሴ ሁሉ ቀጥ ብሏል:: ከቤትና ቤተሰብ ርቄ ያለሁ በመሆኔ እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ በዚህ ያመትባል ዋዜማም ጥልቅ ድብርት እየተሰማኝ ነው:: ላደለው የአዲስ ዓመት ዋዜማ ልዩ ቀን ነው:: ጥፍጥናው ከዋናው አመትባል የሚልቅበት ግዜ ይበዛል…….

በተረፈ ነገ ሌላ ቀንና አመት ነው:: ይህን እመሰክራለሁ::


መስከረም 1 1988 እንቁ ለጣጣሽ!
“አበባዮሽ ቁሙ በተራ እንጨት ሰብሬ ቤት እስክሰራ” የሚለውን የዚህን አመትባል የእንስቶች ተወዳጅ ዘፈን አስታወስኩ:: በተለይም ሁለተኛው ስንኝ ከኔና ከአብሮ ተማሪ ዋደኞቼ ፊት ለተደረደሩት የአምስተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርት  ወሳኝ ወራት ጥሩ መግለጫ ነው:: ሁላችንም ዘንድሮ እንጨት ሰብረን ቤት መስራት ይጠበቅብናል……
  
እንቁጣጣሽ ለት አየሩ የሚደብር አልነበረም:: ጥሩ መልካምና ብራ ቀን ነበር:: ጠዋት እንደተለመደው ከጉዋደኞቼጋ ወይዘሮ አልማዝ ቤት ሂደን እንኩዋን አደረሳችሁ ካልን በሁዋላ የደንቡን ባህላዊ ዶሮ ወጥ ምግብ ተመገብን::  ከዚያም እየተጫወትን በዚያ ቆየን:: ከሰአት ምሳ ዘውድነህ ቤት ተጋብዤ ነበር:: ዛሬ መቸም የመብልና የመጠጥ ቀን ነው:: ዘውድነህ የተማሪዎች ዲን ቢሮ ሃላፊ ነው:: ዘውድነህን የተዋወኩት በተሰፋሁነኝ በኩል ነው:: በዘውድነህ ቤት ዶክተር ተስፋም ነበር የዘውድነህ ባለቤትም እንዲሁ:: ቆንጆ ያመትባል ምግብ ተዘጋጅቶ ነበር:: ብዙ ጠላ በመጠጣቴ ደክሞኝ ስለነበር ከዚያ እንደተመለስኩ መኝታ ክፍሌ ገብቼ ተኛሁ::

መስከረም 2 1988 ሮብ
ሁሉም ነገር ወደነበረበት ተመለሰ:: አመቱ ብቻ ተለውጧል:: ስለዚህም ማጥናት ነበረብኝ:: ዛሬ Fluid and Electrolyte Managementንዲሁም Breast Diseases ለማንበብ ሞክሬ ሁለቱም ጭብጦቻቸው በቀላሉ አልፈታና አልገለፅ ብለውኝ ስለነበር ተበሳጭቼ ዋልኩ::

መስከረም 3 1988 ሃሙስ
ዛሬ ቀን እንዴት Femoral Hernia በቀዶ ጥገና እንደሚስተካከል እየረዳሁ አየሁ:: በምሽቱ በድንገተኛ ክፍል ተመድቤ ነበር:: ኢንተርንሺፕ ሃኪሞች ባጋጣሚ ባለመኖራቸው የነሱን ስራ ተክቼና ሙሉ በሙሉ ራሴን ችዬ የመስራት እድል አጋጥሞኝ ነበር:: በመሆኑም ለመጀመሪያ ግዜ በሽተኛን ወደ ህሙማን ክፍል ገብቶ እንዲታከም አዘዝኩ:: ረዥሙን ፊርማዬን ካርዱ ላይ በማኖር ህመምተኛን ኣድሚት  (Admit) አደረኩ:: ለመጀመሪያ ግዜ የወሰንኩት Clinical Decision…. ከባድ ውሳኔ ነው::  ግን ደስ አኝ:: ወንዳታ አልኩት ራሴን:: ህመምተኛዋ 10 ወር ህጻን ስትሆን በሳምባ ምች (Brncopneumonia) ነው የመጣችው:: እብቅ እብቅ ትተነፍሳለች:: በትንፋሽ ማጠር ምክንያት የእናቷን ጡት መጥባት አልቻለችም:: የሳንባ ራጅ አዝዤ ተሰራላት:: ራጁ ተሰርቶ መጣ:: አየሁት:: ሳምባዎችዋ ሙሉ በሙሉ በደዌው ቆስለዋል:: “በደምስር የሚሰጥ ጸረ ተውሳክ (Antibiotic)ና ኦክሲጂን ባስችኩዋይ ያስፈልጋታል” አልኩዋቸው  ለእናቷና እናቷን አጅበው ለመጡት ቤተዘመዶች :: ስለዚህ በህፃናት መኝታ ከፍል ቆይታ መታከም አለባት:: በኔ ውሳኔና ትዕዛዝ መሰረት ሚጢጢዋ ፍጥረት በእናቷ እቅፍ ውስጥ ሆናና በቤተዘመድ ታጅባ ወደ ሕፃናት መኝታ ክፍል ስትወሰድ እያየሁ……”እውነት ነው?” አልኩ በውስጤ


Sunday, November 6, 2016

ከነሐሴ 28 እስከ ጳጉሜ 5 1987 አ.ም.

በሳምንቱ መጀመሪያ እሁድ  ላይ አንድ ከአዲሳበባ በቅርብ የመጣና ለጊዜው ስራው ጅማ የሆነ ጉዋደኛዬ ባደረገልኝ ግብዣ መሰረት ከሰአቱን ከእርሱጋ አሳለፍኩ:: በመሰረቱ ጥሩ ምሳ ከበላን በሁዋላ እርሱ መኖሪያ ቤት ወለል ላይ በተዘረጋ ቀጭን ፍራሽ ላይ ዘና ብለን ተቀምጠን ንቃተ ህሊናችንን በአረብ ተራ ጫት ቀንበጥ የበለጠ አንቅተን ቧልት የተቀላቀለበት ፍልስፍና ስንሰልቅና የተለያዩ የእንግሊዝኛ ሙዚቃዎች ስናዳምጥ ዋልን:: በጣም የምቀርባቸውና የምወዳቸው ሁለት ጉዋደኞቼ መንጌና አብይ አብረውኝ ነበሩ::

በማግስቱ ሰኞ በቀደመው ሳምንት የነበረኝን ሕክምና የመማር ልበሙሉነትና ተነሳሽነት የሚያሰርዝ ሁኔታ ገጠመኝ:: ከህሙማኖቼ መካከል አንደኛው  የእግሩ ጡንቻ በሰፊው በመምገሉ (pyomyositis) ጉልበቱና ብሽሽቱ ላይ መሸማቀቅ ደርሶበት እግሩ ባጠቃላይ መዘርጋት አልቻለም (Contracture):: ለዚህ ህመምተኛ የእግሩን ቆዳ በሰፋፊ የቁስል ፕላስተር በመለጠጥ እግሩ እንዲዘረጋ ለማረግ (Skin traction) አስቤ ግን ከዚህ በፊት ሰርቼው የማላውቅ ነገር በመሆኑ ሳልፈፅመው አደርኩኝ::

ማክሰኞ ቁጥር 6 አልጋ ላይ አዲስ ህመምተኛ ነበረኝ:: አንድ ቁመቱ አጭር ሰውነቱ የፈረጠመ  ሰው ነው:: ግራ ደረቱ ላይ አንበሳ ቦጭቆት ነው ወደ ሆስፒታሉ የመጣው:: አንበሳ ፔክቶራሊስ ሜጀሩንና ማይነሩን (Pectoralis major & minor) ገሽልጦ ሰልቅጦታል:: በአንበሳ የተነከሰ ሰው ለመጀመሪያ ግዜ ማየቴ ስለነበር ሰውዬውን  ራሱ እንደ አንበሳ እየፈራሁ ነው ያናገርኩት:: ሰውዬው ፈርጣማ በመሆኑ ነው መሰል የግራ ደረት ጡንቻው ከቦታው ከመጉደሉ በስተቀር ሌላ የህመም ምልክት ሳይታይበት አንዳልታመመ ሰው ነው ያነጋገረኝ:: ይህ ሰው የሚኖርበት አካባቢ በቅርብ ርቀት አንበሶችም እንደሚኖሩና እሱን የነከሰችው  ሴት አንበሳ መሆኗን ነገረኝ:: አንበሲቷ እየነከሰችው  ሳለ ጎረቤቶች ደርሰው አስጣሉትና ይዘውት ወደ ሆስፒታሉ መጡ:: ቁስሉ በድንገተኛ ክፍል የመጀመሪያ እርዳታ ከተደረገለት በሁዋላ ወደመኝታ ክፍል የመጣው በዋናነት ፀረ ህዋስ መድሃኒት (Antibiotic) በደም ስሩ መሰጠት ስላስፈለገው ነው::

እሮብ ጳጉሜ አንድ ቀን ከቤት የላክልኝ ሃምሳ ብር ከእናቴ የደመቀ ሰላምታ ጋር ደረሰኝ:: ይህ በሆነ በሶስተኛው ቀን ቅዳሜ ጳጉሜ 04  ከኛ በሁለት ዓመት የሚበልጡን ሐኪሞች (the 1987 graduates) በመመረቃቸው  በጅማ ሆቴል ያዘጋጁትን የምሽት ዳንኪራ ስካፈል ሃምሳ ብሬንም በሆቴሉ ውስጥ ላለው ባር አካፈልኩ :እነሱም መጠጥ አካፈሉኝ: የኔም ራስ ለሁለት ተከፍሎ ከውድቅት ወዲያ ወደመኝታ ክፍሌ ደረስኩ::


እሁድ ጳጉሜ 5ን በሃንጎቨርውስጥ አሳለፍኩ:: የዚህ ዓመት ጳጉሜ 6 ቀን በመሆኑ እሁድ አዲስ ዘመን ዋዜማ አልነበረም:: 

Wednesday, November 2, 2016

የቀዶ ጥገና አንድ ሳምንት ነሐሴ 22 -26 1987 አ.ም.

ሰኞ ነሐሴ 22 ቀን 1987 አ.ም.
እኔና እኔ ያለሁበት ቡድን ዛሬ በጠዋት የአምስተኛ ዓመት የቀዶጥገና (Surgery) አታችመንት ጀመርን:: በደፓርትመንት ኃላው በዶ/ር አለምሰገድ ቢሮ ተገኝተን ከእርሱ መመሪያና ምክር ተቀበልን::  ዶ/ር አለምሰገድ ሰባት ሳምንት በሚፈጀው ቀጣዩ የቀዶ ጥገና ልምምድና ሥራ (attachment) የሚከናወኑ ተግባራትና ከኛ የሚጠበቀውን ዝግጅት አስረዳን:: የመጨረሻ ዓመት ላይ የምንገኝ በመሆኑ ጠንክረን እንድናጠና አስጠነቀቀን::  በዚህ እለት ከምሽቱ አንድ ሰዓት ላይ ወደ ሆስፒታሉ የቀዶ ጥገና መኝታ ክፍል በመሄድ የተመደቡልኝ ህሙማን ተዋውቄና በማግስቱ ተመልሼ እንደማያቸው ቃል ገብቼ ተመለስኩ:: አሁን እንደአምናው በሽተኛ መቅረብ በፍፁም አይከብደኝም:: አራተኛ ዓመት ሲጀመር የመጀመሪያውን ህመምተኛ ለማናገር የነበረኝን ፍርሃት እስካሁን አልረሳውም:: ዛሬ ሁሉ ቀላል ነው:: ደሞ ህመምተኛ ማናገር ምን ይከብዳል?

ማክሰኞ ነሐሴ 23 ቀን 1987 አ.ም.
ዛሬ ከዶ/ር ግዛውጋ ቀላል ቀዶ ጥገና አደረግን Herniotomy & Hernioraphe of Epigastric Hernia:: ለመጀመሪያ ግዜ በቀዶ ጥገና ግርዛት (Circumcision) ያየሁትም ዛሬ ነው:: ከሰዓት በሁዋላ ወደ ሆስፒታሉ የቀዶ ጥገና መኝታ ክፍል በመሄድ የተመደቡልኝን ህሙማን በሙሉ መርምሬና መዝገባቸውን አገላብጬ እንዲሁም የበኩሌን ዘገባ ስለእያንዳንዳቸው ፅፌ አጠናቀኩ:: ለነገ ተዘጋጀሁ::

ረቡዕ ነሐሴ 24 ቀን 1987 አ.ም.
ዶ/ር ግዛው ዛሬ ሁሙማኑን በሙሉ እየዞረ ጎበኘ: መረመረ:: እኛም ስለህመምተኞቻችን የዘገብነውን አነበነብንለት:: ይሆናል ያልነውን የላቦራቶር መርመራና አስፈላጊ ሕክምና ጠቆምን: ተናገርን:: እሱም አንዳንዱን ሲከለክል አንዳንዱን ደግሞ ይሁን አለ:: የከለከለውንም ለምን እንደከለከለ አስተማረ:: ከዚያም ከሰዓት ሆነ:: ዘመኑ እና ዮናስ የሚባሉት የኔ ቡድን አባላት ሴሚናር አዘጋጆች ነበሩ:: ይህ በሆነ አርስት ላይ መፅሐፍ አገላብጦና አንብቦ ለታዳሚ የሚቀረብበት ዝግጅት ነው:: በዝግጅቱ መጨረሻ ላይ ታዳሚ ከበድ ያለ ጥያቄ ሊሰነዝር ይችላልና አቅራቢ ሲኮን ያሳስባል:: ዘመኑ እና ዮናስ ዶ/ር አለምሰገድ ባለበት አቀረቡ:: ምንም የተለየ ነገር ሳይኖር ተጠናቀቀ:: በዚህ ቀን ምሽት በቀዶ ጥገና ድንገተኛ ህሙማን የሚታዩበት ክሊኒክ ውስጥ ተረኛ ነበርኩ:: እስከምሽቱ ሶስት ሰዓት ተኩል በዚያ ቆየሁ::

ሐሙስ ነሐሴ 25 ቀን 1987 አ.ም.
በዚህ ቀን ደግሙ ከባድ ቀዶ ሕክምና ክፍል (Operating Theatre) ውስጥ ነበርኩ:: ሁለት ቀዶ ጥገናዎች ተደረጉ:: አንደኛው የሆድ ቀዶ ጥገና ሲሆን ህመምተኛዋ ለአንድ አመት ያክል ግዙፍ እባጭ በሆዷ ተሸክማ የቆየች ናት::  ሌላኛው  አንዲት ትንሽ ሴት ሕፃን ልጅ እጇን አንድ አዋቂ ሳያስበው በመጥረቢያ ቆርጦት ነው:: ታሪኩ ቢዘገንነኝም ቁስሏ ሲሰፋና ሲዘጋ እያገዝኩ ተመለከትኩ:: ታዲያ ዛሬ ቀዶጥገና ከሕክምና ትምህርቶች ሁሉ የሚስብ ሆኖ ታየኝ:: ቅፅበታዊ ቀዶ ጠጋኝ የመሆን ፍላጎት አደረብኝ:: ለዚህም ነው ቀዳጁን ዶ/ር ሚናስን አራተኛ ዓመት እያለሁ በጣም የተደሰትኩበት የህክምና ትምህርት ምን እንደሆነ ሲጠይቀኝ ቀዶ ጥገና! ብዬ የመለስኩለት:: እሱም በጣም ከት ብሎ ሳቀ:: መልሴ የታሰበበት እንዳልሆነ ገብቶታል::


አርብ ነሐሴ 26 ቀን 1987 አ.ም.

ዛሬ ጠዋት በታማሚ አልጋ ዙሪያ ቆመን የምንማርበት ከፍለግዜ (Bed Side) ነበረን:: ህመሙ Gastric outlet obstruction (GOO ብለን አሳጥረን የምንጠራው) ነበር:: አስተማሪው ቀዳጅ ሀኪም ዶ/ር ሚናስ ነበር:: ከሰዓት በሁዋላ ደግሞ ክፍል ውስጥ ቁጭ ብለን ስለ አንድ በሽታ ሕክምና በቻ በጥልቀት የምንወያይበት ክፍለግዜ (Management Session) ነበር:: ትምህርቱ ጅማ ሆስፒታል ውስጥ ተኝቶ እየታከመ ያለ ወይም ታክሞ የነበረ እውነተኛ ህመምተኛ ላይ ተንተርሶ የሚሰጥ ነው:: የዛሬው ያተኮረው a case of traumatized patient and head injury ላይ ነበር:: አስተማሪው ቀዳጅ ሀኪም ዶ/ር ግዛው ነበር::

Sunday, July 10, 2016

ሰኔ 2 ቀን 1987 አ.ም.

ዛሬ ለምን እንደሆነ ባላውቅም ፅሁፌን በዚህ እጅግ መንፈሳዊ ሐረግ እጀምር ዘንድ ውስጤ አለኝ: በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሃዱ አምላክ አሜን!

በዚህች ቅፅበት የምገኘው አዲስ አበባ ቀራንዮ መድኃኔዓለም አካባቢ በሚገኘው መኖሪያ ቤታችን ሳሎን ውስጥ ካለችው አነስተኛ ታጣፊ አልጋ ላይ ተቀምጬ ነው:: አራተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርቴን አጠናቅቄና ወደአምስተኛ ዓመት መሸጋገሬን አውቄ ከሚያዚያ 28 ጀምሮ በእረፍት ላይ እገኛለሁ:: እስከ ሰኔ 28 ቆይቼ ወደ ጅጤሳ እመለሳለሁ::

ይህን የማስታወሻ አጀንዳ አንድ ጉዋደኛዬ በራሱ አነሳሽነት ሰጠኝ:: እሱ ይሕን ባያደርግ ኖሮ ማስታወሻ ሁለተኛ ላለመፃፍ ወስኘ ነበር:: አሁን ግን ሃሳቤን ቀየርኩ::  ከጊዜ ወደ ጊዜ ማስታወሻ መፃፍ እየታከተኝና አስጠሊታ እየሆነብኝ ቢመጣም ምናልባት አምስተኛ ዓመት ከኢንተርንሺፕ በፊት የመጨረሻው የህክምና ትምህርት ዓመት ስለሆነ የብዕር ሚዛን የሚደፋ አጋጣሚ አይጠፋው ይሆናል በሚል ለመፃፍ አሰብኩ::

የዘንድሮ እረፍት ባጠቃላይ ሲታይ ምንም አይልም:: ደህና ነው:: አንዳንድ ግዜ ብቻ ቀኑ አልሄድ ይላል:: የሚገርመው ነገር ያሳለፍኩት ግንቦት ወር ባልተለመደ ሁኔታ ብርዳም ነበር:: ከዚህ ብርድ ይሁን ከሌላ ምክንያት ጤንነቴ የጠራ አልነበረም:: ሰውነቴን ለምን በጣም እንደማዳምጥ አይገባኝም:: በየቀኑ ቁርጥማት ይሰማኛል:: በተደጋጋሚ ይደክመኛል:: ራሴን ቅልል ቅልል ይለኛል:: ሆዴን ያመኛል:: እንቅልፍ በደንብ አልተኛም:: መተኛት ራሱ ያደክመኛል:: ሽንቴ ከቀድሞ ይልቅ አሁን ቶሎ ቶሎ ይመጣል:: ሌሊት ቢያንስ ሁለት ግዜ ለመሸናት ከአልጋዬ እነሳለሁ:: ውሃም ቶሎ ቶሎ ይጠማኛል:: ቆዳዬ ያለወትሮው እንደ መድረቅ ብሏል::  እግዚአብሔር ከክፉ ነገር ይሰውረኝ::

ሐምሌ 3 ቀን 1987 አ.ም.

ዛሬ ጠዋት ሶስት ሰዓት ላይ የአምስተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርት ሀ ተብሎ ተጀመረ:: ዶክተር ዳመና የሚባል ያንገት በላይ ቀዳጅ ሀኪም የጉሮሮ: የጆሮና የአፍንጫ ሕክምና ለሁለት ሳምንት ሊያስተምረን ዛሬ ጀመረ:: ይህ እንግዲህ አናሳ (Minor) ኮርሶች ከሚባሉት ውስጥ አንዱ መሆኑ ነው:: በበኩሌ በአናሳ ኮርስ አመቱን መጀመራችን ደስ ነው ያለኝ:: ለደምበኞቹ ኮርሶች ገና አልተዘጋጀሁም::


ዘንድሮ በአንድ ዶርም ውስጥ 12 ሆነን እንድኖር ስለተደረገ ካምናው ይልቅ በዶርሙ ውስጥ ከፍ ያለ ግርግር አለ:: ጥበትና ትርምስ ይንፀባረቃል:: ማታ-ማታ በጣም በምፈልገው ፀጥታ ፋንታ ጫጫታ ይነግሳል:: ለማንበብ ቀርቶ በእርጋታ ለማረፍ እንኩዋን አይመችም:: 12 ሆነን በአንድ ዶርም እንድንኖር የተደረገው ጅጤሳ አዲስ የዲግሪ መረሃ ግብሮችን በመዘርጋት ተጨማሪ ነርሶችን: ላቦራቶሪ ቴክኒሻኖችንና ሳኒተርያኖችን ለማስገባት በማቀዱ ይመስለኛል:: ዋይት ሃውስ ህንፃ በመሰከረም ወር በጣም እንደሚጣበብ እገምታለሁ:: 

Sunday, June 26, 2016

ጥቅምት 15 ቀን 1987 አ.ም

አራተኛ ዓመት አጋማሽ
አራተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርት ከተጀመረ አምስት ወር ሆነው:: እግዚአብሔር ይመስገን አሁን በስቴቶስኮፔ በማዳመጥ ከወትሮ የተለዩ የሰውነት ውስጥ ድምፆችን መለየት ችያለሁ:: በሽተኛን በእጄ እየደባበስኩ (palpation) ከወትሮው የተለቀ ጉበትና (Hepatomegally) የረዘመ ቆሽት (Splenomegally) በፍጥነት መለየት ችያለሁ:: ባለፉት አምስት ወራት ያለፍኩባቸው የቀዶ-ጥገናም (Surgery) ሆነ የውስጥ-ደዌ (Internal Medicine) ተግባራዊ ልምምዶች (Attachments) መልካም ነበሩ:: እንደፈራሁዋቸው ከባድ ወይም ስንክሳር የበዛቸው አልነበሩም:: ክፉና ተቆጪ መምህር አልገጠመኝም:: ባለፈው የጠቀስኩትን በሽተኛን አገላብጦ የመመርመር ፈተና የፈተነኝ ዶክተር ሳዲቅ እንኩዋን እንደገና በውስጥ-ደዌ ተግባራዊ ልምምድ  ስንገናኝ ፈፅሞ የተለየ ሰው ነው የሆነብኝ:: እንዲያውም በጣም የተረጋጋ: መካሪና ታላቅ ወንድማዊ ሆኖ አገኘሁት::

በነዚህ እያንዳንዳቸው አስር ሳምንታት በፈጁ ተግባራዊ ልምምዶች ወቅት የገጠመኝ አንዳችም የተለየ: ወይም ያልተጠበቀ ነገር አልነበረም:: ሁለቱንም ልምምዶች ስንጨርስ ተግባራዊ ፈተና (Practical Exam) ወሰድን:: ፈተናዎቹ እውነተኛ በሽተኞችን በሽታቸውን ጠይቆና መርምሮ: ለሚፈትነው መምህር የህመማቸውን ምንነት (Diagnosis) እንዲሁም በሽታውን ለማጣራት መደረግ ያለባቸውን የላቦራቶርም ሆነ የራጅ ምርመራ አይነቶችን (Diagnostic Tests) መዘርዘር ይጠይቃሉ::  ጥያቄና መልሱ የሚካሄደው እዚያው በሽተኛው የተኛበት አልጋ በቀኝ በኩል በመቆም ነው:: ፈታኙ መምህር በቦታው ከመድረሱ በፊት በሽተኛውን ለማነጋገርና ለመርመር የአንድ ሰዓት ጊዜ ይሰጣል::

በሁለቱም ፈተናዎች የደረሱኝ  የተለመዱና ቀለል ያሉ ኬዞች (Cases) ነበሩ: የውስጥ-ደዌ ፈተና በጉበት ታማሚ ላይ ሲሆን የቀዶ-ጥገና ደግሞ ሽንቱን መሽናት ባቃተው ታማሚ  (A  case of urinary retention) ላይ ነበር:: ባጠቃላይ ፈተናዎቹ  በጥሩ ሁኔታ ነው የሄዱት: ውጤቱን ግን እግዚአብሔር ነው የሚያውቀው::

ዛሬ ደግሞ የፅሁፍ ፈተና ወሰድን:ቀዶ-ጥገና. ቀለል ብሎ ተሰማኝ:: እርግጠኛ አይደለሁም ግን ምናልባት ፈተናው ከባድ ሆኖ እኔ ክብደቱን ማወቅ ተስኖኝ ሊሆንም ይችላል.....ለውስጥ-ደዌ ፈተና የፊታችን አርብ እንቀመጣለን:: ከዚያ በሁዋላ የሁለት ሳምንት እረፍት ይኖረናል:: እኔም ወደ አዲስ አበባ እሄዳለሁ::


ቅዳሜ መጋቢት 16 1987 አ.ም.

ሞሚናና የ አራተኛ ዓመት መጨረሻ
ዛሬ በጣም ያዘንኩበት ቀን ነው:: በጣም የምወዳትና የማከብራት እጀግ በጣም የቅርብ ጉዋደኛዬ ሞሚና የነርሲንግ ትምህርቱዋን አጠናቃ እኔንም ሆነ ጅጤሳን ተሰናብታ ሄደች:: ሞሚናን በጣም አቀርባት: በመልካምነቱዋ እወዳትና ከሁሉም በላይ ደግሞ በሥራዋ : በአላማዋ አከብራት ነበር:: ሞሚና ልክ እንደኔ የአማርኛ ስነ-ፅሁፍ በተለይም ግጥም ትወዳለች ትፅፋለችም:: ለሌሎች ሰዎች ጥሩ ነገር የማድረግ ጥማት አላት:: አብረዋት የተመረቁት የነርሲንግም ሆነ የሌላ ዘርፍ የዲፕሎማ ተማሪዎች በውስጣቸው በተፈጠሩ ጥቃቅን አለመግባባቶች የተነሳ በጋራ አንድ የምረቃ መፅሄት ማሳተም ተስኖዋቸው ሳለ ሞሚና ግዜዋን (ገንዘቡዋንም ይመስለኛል) ሰውታ የተራራቁትን ተመራቂዎች አስተባብራ ግሩም የሆነ መፅሄት እንዲታተም አድርጋለች:: በመፅሄቱ ውስጥ ከሰፈሩት ፅሁፎች ውስጥ አየነው በተባለ ተመራቂ የተፃፈ C'est la vie (That is Life) የተሰኘ የእንግሊዝኛ መጣጥፍ አይረሳኝም:: ከኔ ሌላ ብዙ ፅሁፉን ያነበቡ ተማሪዎች ሲያደንቁት ሰምቻለሁ::


ሞሚና ተሰናብታኝ ስንለያይ ሆዴ ውስጥ የሆነ ነገር ሲራወጥ ተሰማኝ:: በተለይ ደግሞ ከምረቃው (Graduation) ቀን ጀምሮ እስከዛሬ ባሉት ቀናቶች በተደጋጋሚ  አብረን ያሳለፍናቸው የሻይና የቡና ጊዜያት አይረሱኝም:: እንደወትሮአችን ሁሉ ብዙ ነገሮችን አወጋን:: ሞሚናን የተለሁበት ወቅት የአራተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርቴን ለማጠናቀቅ ፈተና ለመውስድ ሽር ጉድ የምልበት ወቅት በመሆኑ የኔን ሁኔታ ከባድ አድርጎታል:: ለመጨረሻ ጊዜ ያገኘሁዋት ዛሬ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ገደማ መንሱር ሱቅ አጠገብ ነበር..........

Sunday, June 5, 2016

ሰኔ 21 ቀን 1986 አ.ም.

ሀኪም ወደመሆን…

የኔ ዉድ: ያን የሶስተኛ ዓመት መጨረሻ ገደማ የህክምናን ትምህርት ቀጥሎ የማጠናቀቅ ፅኑ ውሳኔ በልቤ ማኖሬን የሚጠቅስ ማስታወሻ ካሰፈርኩበት ቀን በሁዋላ: ምንም ለትውስታ የሚበቃ ክስተት ሳይኖር: ቀናቱ እንዴት እንደሄዱ ሳላውቀው: ራሴን የአራተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርት (C-1) መጀመሪያ ሰሞን አገኘሁት:: ለመጀመሪያ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያዊ በሆኑ ዶክተሮች ብቻ  ሕክምናን የምንማርበት: እውነተኛ የታመመ ሰው የምናነጋግርበት እንዲሁም የምንመረምርበት ዓመት….. ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ቀልድ አያውቁም:: ኩሩዎች: ቁጡዎችና ግሳፄያቸው የሚያስፈራ ናቸው:: በየጊዜውና በየሁኔታው ይገስፁናል:: በእውነቱ ሐኪምም ቢሆኑ እነዚህ የሚመቹኝ እንደማይሆኑ ግልፅ ነው:: በእርግጥም አልተመቹኝም:: እነሱ ሲገስፁ እኔ ሲጎረብጠኝ: እነሱ ሲገስፁ እኔ ሲጎረብጠኝ: አራተኛ ዓመት በተጀመረ በአንድ ወሩ የተሰጠኝን በሽተኛን አገላብጦ የመመርመር (Physical Exam) ፈተና ሳላልፍ ቀረሁ:: ማለትም የተዘጋጀልኝን በሽተኛ ከበስተጀርባዬ እንደጅብራ ቆሞ ሲያየኝ ለነበረው ሀኪም(ዶ/ር ሳዲቅ) በሚያረካ መልኩ ሳላገላብጠው: ሳልመረምረው ቀረሁ:: መርምሬውም ዶ/ር ሳዲቅ ከኔ ቀድሞ በሽተኛውን መርምሮ ያወቀውን እኔ ሳላውቅ ቀረሁ:: ዶ/ር ሳዲቅ ሀበሻዊ ቁጣን ተቆጣ:: ገነፈለ:: ዘራፍ አለ:: በሽተኛው ብልብና ትንፋሽ ማዳመጫው (stethoscope) የሚሰሙ: ከሳንባዎቹ የሚፈልቁ ቀጫጭን የስትንፋስ ድምፆች (bronchial  breath sounds) ነበሩት ለካ….የሳምባ ምች (Pneumonia) ተጠቂ ነበር::

ከዚህ አጋጣሚ በሁዋላ መንፈሴ ትክክል አልነበረም:: ከማንም ጋር ማውራት አልከጀልኩም:: ብቻ ቀጥታ ወደ ማደሪያዬ በማቅናት: ፊቴን ወደ ግድግዳው አዙሬ አልጋዬ ላይ ተጋደምኩና: የአይኖቼን ቀዳዶች ፈንቅሎ ሊወጣ የሚዳዳውን ንዴት አዘል እምባ ታገልኩት...

Sunday, May 29, 2016

ህዳር 7 1986 አ.ም.

የንቃት ጅማሬ
ትናንትና በድንገት ከቅርብ ጉዋደኛዬጋ ፍራሽ ላይ ተቀምጬ የጅማን ጫት በአፌ ውስጥ አኖርኩ: : በሂወቴ ጫት ስነካ የመጀመሪያዬ ነው:: ጫቱን አፌ ውስጥ አስገብቼ አኘኩት: እኛኪውንም መጠጥኩት:: እኔና ጉዋደኛዬ ከፊትለፊታችን ፍራሹ ላይ ግማሽ እግሮቻቸው ባለ አስር ሳንቲም ፌስታል ውስጥ ያረፉ የጫት ዝንጣፊዎችን  በግራ እጆቻችን በመያዝ በቀኝ እጆቻችን ቀንበጦቹን አሁንም አሁንም ወደ አፎቻችን በማስገባት አሻመድናቸው:: በቀንበጦቹ ድዶቻችንን አስታከን ለጋ ጉንጮቻችንን ወጠርናቸው: ለተወሰኑ ደቂቃዎች በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ አወጋን:: ቧልት እየቦለትን ተሳሳቅን:: አንዳንድ ያጋራ የሆኑ ምናባዊ ሀስቦቻችንን ተለዋወጥን::ከዚያም ፊቶቻችን መሞቅ: ማብለጭለጭና መቅላት ጀመሩ:: አፍታም ሳንቆይ ነቃን:: ወጣት አእምሮዎቻችን ለአትኩሮት ተዘጋጁ:: የእጅ, የእግርና የወገብ ጡንቻዎቻችን ተፍታቱ:: ወደ pathology ንባባችን ገባን:: በበኩሌ ሃሳቤ ተሰባስቦ ካነበብኩባቸው ጥቂት የሚታወሱ ቀናት ይህ አንዱ ነው::

በትናንትናው የጥናት ስኬት በመነሳሳት ታዲያ ጫትን ዛሬም ደገምኩት:: ነገር ግን ውጤቱ እንደንትናንትናው ሊሆን አልቻለም:: አለመሆን ብቻ ሳይሆን እንደ ድካም: እንደመዛል አድርጎ ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ወሰደኝ: ከቀኑ ሰባት ሰዓት የተኛሁ አስር ሰዓት ላይ ተነሳሁ:: ከዚያም ወደ ቤተ መፅሃፍቱ በመሄድ እስከምሽቱ ሶስት ሰዓት ድረስ አጠናሁ...የእንቅልፉ ነገር ቢገርመኝም ህዳር 8 ቀንም እንደቃምኩ ግን ልብ በል/ይ...የሆነ ጥቅም ያለው መስሎ ተሰምቶኛል...

ህዳር 17 ቀን 1986 አ.ም.

የልቤ ወግ
እንደምን አለሽ ማስታወሻዬ:: እኔ መችም አለሁ:: ምንም አልልም:: በሶስተኛ ዓመት የበረታው የልቤ መከፋት እንደቀጠለ ነው:: ይህን ስል ግን በጉዋደኞቼም ሆነ በሌሎች ሰዎች ፊት ደስታኛና መልካም መስዬ መቅረቤ እንደቀጠለ መሆኑን ላስታውስሽ እወዳለሁ ::

ልቤን በብርቱ እያስከፋው ያለው ነገር የሶስተኛ ዓመት ህክምና ትምህርት የፈተና ውጤቶቼ ከከዚህ ቀደሞቹ አንፃር አመርቂነት እያነሳቸው መምጣቱ ነው:: የዚህ ዋናው ምክንያት ግልፅ ነው: በንባብና በጥናት አለመትጋቴ ነው:: ለማወቅ የከበደኝ ግን ለምን እንደማልተጋ ነው:: በውስጤ ግዙፍ የሆነ የትምህርት ፍላጎት ማነስ አለ:: እስካለፈው ሰሞን ድረስ ቀዶ ጠጋኝ ሀኪም ( surgeon) ለመሆን እመኝ ነበር::  አሁን ግን ይህ ምኞት እውነተኛ ምኞቴ እንዳልሆነ ሆኖ ተሰማኝ:: ስለዚህም አዳፈንኩት:: አሁን በቃ የህክምና ትምህርቴን ለመጨረስ ብቻ ነው የማስበው:: ከዚያ በሁዋላ ወደ ስነ-ጥበብ (Art) ለመግባት ሕልም አለኝ:: ይህ ሕልም አሁን የተፈጠረ አይደለም:: እኔ ሃይስኩልም ሆነ ከዚያ በታች ስማር በነበረበት ወቅት በግጥም ገጣሚነት: በድርሰት: በስእል: እንዲሁም በዘጋቢነት የጎላ ተሳትፎ ነበረኝ:: እንደውም አንዳንድ መምህራንና ጉዋደኞቼ የከፍተኛ ትምህርቴን ከሳይንስ ይልቅ በአርት መንገድ እንዳደርገው መክረውኝ ነበር:: ለምን በአርት መንገድ እንዳልሄድኩ በውል አላውቀውም:: ነገር ግን ባዮሎጂ : ፊዚክስና ሂሳብ ትምህርቶችን ጥልቅ በሆነ ፍላጎት (passion) እወዳቸው እንደነበር አውቃለሁ:: ሳይንስ ተጨባጭ ስለሆነ ይመቸኛል:: ከሳይንስ ትምህርቶች ውስጥ ሕክምናን እንድመርጥ ተፅዕኖ ያሳደሩብኝ ሶስት ሁኔታዎች ይመስሉኛል:: አንደኛ ባደኩበት አካባባቢም ሆነ ከዚያ በሰፋው ማህበረሰባችን ሕክምናና ሀኪም የተሰጣቸው አክብሮትና ስፍራ የትየለሌ መሆኑ: ከዚህ በፊት እንዳልኩት ጮርቃ ልጆች ሆነን ስታድግ/ጊ ምን ለመሆን ነው የምትፈልገ/ጊው ተብለን ስንጠየቅ ብዙዎቻችን የምንመልሰው “ዶክተር” ብለን ነበር:: ሁለተኛው ምክንያቴ የአስራሁለተኛ ክፍል መልቀቂያ በሆነው የማትሪኩለሽን  ፈትና ባዮሎጂና ሂሳብ “A” ነገር ግን ፊዚክስ “B” ማግኘቴ ነበር:: ከሶስቱ የምወዳቸው ትምህርቶች ወስጥ ፊዚክስን የበለጠ ነበር የምወደው:: ነገር ግን ይህን የፈተና ውጤት ካገኘሁ በሁዋላ ቆም ብዬ አሰብኩ:: በዚህ ምክንያት ኢንጂነሪንግ ወይም አራት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ምርጫዬ ሳይሆን ቀረ:: ሶስተኛውና በመጨረሻው ሰዓት ላይ ተፅዕኖ ያሳደረብኝ የትምህርትቤቴ (የአዲስከተማ) ተማሪዎች ዲን የነበረው ሰው (ስሙን ሳልረሳው አልቀረም ግን መኩሪያ ይመስለኛል)በማትሪክ ጥሩ ውጤት ያመጣነውን ተማሪዎች ሰብስቦ የተናገረን ነገር ነው:: በትክክል ቃል በቃል ባላስታውሰውም  እንዲህ ያለ ይመስለኛል:: “ውጤታችሁ 3.6ና ከዚያ በላይ በላይ የሆነ ተማሪዎች ሜዲስን ትምህርት መምረጥ አለባችሁ: ከባድ ቢሆንም በጥሩ ሁኔታ ትወጡታላችሁ የሚል ከፍተኛ እምነት አለኝ:: ሌሎቻችሁ ግን ከሜዲስን ውጭ የሆኑ ትምህርቶች ላይ አተኩሩ::” በዚህ አነጋገሩ የሜዲስን ትምህርትን ከባድ ብሎ ቢፈርጀውም ለኔ ልዩ (ብርቅ) አድርጎ አቀረበው:: ለተወስንነው ብቻ የሚሰጥ እንደከበረ ድንጋይ እንደልብ የማይገኝ አርጎ አቀረበው:: ስለዚህም ከላይ ከጠቀስኩዋቸው ሁለት ምክንያቶች ጋር ተዳምሮ በውስጤ በነበረ የተለየውንና ብርቁን  ነገር የመሻት ተፈጥሮአዊ ግፊት ሜዲስንን ለመማር መረጥኩ::

የህክምና ትምህርት በየቀኑ እጅግ በጣም ረዥም ለሆነ ሰዓት በትዕግስት ሃሳብን አሰባስቦ አእምሮን አሹሎ ማንበብን ይጠይቃል:: በእርግጥ ይህን ማድረግ የሚችሉ አንዳንድ ብርቱ ጉዋደኞቼ አሉ:: ጉዋደኞቼ ካልሆኑትም ውስጥ ጎበዝ የምላቸው አንባቢዎች አሉ:: እነዚህ በጅጤሳ አነጋገር “በራቾች” ይባላሉ:: ብረት ከሚለው ቃል የተወሰደ ነው:: ሕክምና ትምህርት ከተነበበ በሁዋላ ደግሞ ማስታወስን ይፈልጋል:: አንብበው የሚያስታውሱ የመኖራቸውን ያህል ብዙ አንብበው ግን በበቂ ሁኔታ ማስታወስ የሚሳናቸው አሉ:: እነዚህ ያሳዝኑኛል:: አንዳንዶች ደግሞ አሉ:: በቃ በቀላሉ የሚገባቸው:: የሚገልፅላቸው:: እነዚህ ብዙ ማንበብ አያስፈልጋቸውም:: ፈተና ላይም የሚችላቸው የለም:: ያስቀናሉ:: በፍጥነት ማንበብ የሚችሉ ደግሞ አሉ:: ቶሎ ቶሎ የሚያንቡትን ደብተርም ሆነ መፅሐፍ ይገልጡታል:: እንደነዚህ አይነቶቹ አጠገብ ተቀምጦ ማጥናት ሰቀቀን ነው:: ከማስደንገጡም ባሻገር የሞራል ውድቀት ሊያስከትል ይችላል::

ታዲያ እኔ የቱ አይነት ነኝ? ለረዥም ሰዓት ተቀምጠው ማንበብ ከሚችሉት ወገን እንዳልሆንኩ መቸም ግልፅ ነው:: ተፈጥሮዬ አይፈቅድም:: በፍጥነት ከሚያነቡት ውስጥም አይደለሁም:: ብዙ የማያነቡ ካሉ እኔ ከነሱ ወገን ነኝ::

ከላይ እንዳልኩት በዚህ ሰዓት የህክምና ትምህርት ፍላጎቴ ክፉኛ ዳሽቁዋል:: ምናልባት ትንሽም ቢሆን ያነበብኩትን አስታውሳለሁ መሰለኝ.......ከሴሚስተር ወደ ሴሚስተር በመሽጋገር ለሶስተኛ ዓመት የመጨረሻ ማጠቃለያ ፈተና ሰሞን ደርሻለሁ::

ሕክምና ትምህርቴን ለመጨረስ ቁርጠኛ ውሳኔን በልቤ አኖርኩ: ዛሬ.....





Sunday, April 3, 2016

መስከረም 2 ቀን 1986 አ.ም.

የልደታ ትዝታ

ትናንት እንቁጣጣሽ ዋለ:: አዲስ ዓመት ገባ:: በዚሁ ቀን ምሽት ላይ ከአብሮአደግ ወዳጆቼ ሳሚ: ዳዊትና ተሾመ ጋ ልደታና አካባቢዋ በመዘዋወር ከቡና ቤት ቡናቤት እየለዋወጥን በመጠጥና በዳንኪራ ራሳችንን ስናዝናና አመሸን:: ይገርማል እንደቀልድ ቡና ቤት ገብቶ መጠጥ መጠጣት ጀመርኩ:: እድሜዬ አሁን 21 ዓመት ነው:: ጅማ በተደጋጋሚ ያደረግሁት ቢሆንም አዲስአበባ ግን የመጀመሪያዬ መሆኑ ነው:: በጣም ደስ ና ደስ ብሎኝ ነው ያመሸሁት:: ከነሳሚ ጋር በገባንባቸው ቡና ቤቶች ሁሉ የሚያጋጥሙን አዲሳቤ ጠጪዎች ወጣትም ይሁን ሽማግሌ: ሴትም ሆነች ወንድ: ሁሉም እንደኛው በሞቅታ ንፍቀ ክበብ ውስጥ የነበሩና ቡናቤቶቹ ማዕዘኞች ላይ ከተሰቀሉት ድምፅ አጉሊ ስፒከሮች ከሚሰሙት ማናቸውም አይነት ዘፈኖች ጋር የሚወራጩ ነበሩ:: አሁን ሳስበው እኔ ራሴ ሞቅ ብሎኝ ስለነበር ነው እንጂ እየተወራጩ ሳይሆን እየደነሱ ነበር:: ቡናቤቶቹ በሰው ከመሞላታቸው የተነሳ ለመደነስ የሚሆን ቦታ ባለመኖሩ ሁሉም ሰው እዛው በቆመበት ነው ይወራጭ  የነበረው:: ወደየትኛውም አቅጣጫ መንቀሳቀስ የሰው እቅፍ ውስጥ ከመዳረግ ባሻገር ያልተጠበቀ ሰላምታና መጠጥ ባሰረው ምላስ "እንኩ..ዋ..ዋ....ን አ...ደደ...ረ..ሰህ/ሽ" መባባልን ያስከትል ነበር:: ከምሽቱ አምስት ሰዓት ሲሆን ሁላችንም ወደነ ሳሚ ቤት በመሄድ አንድ ለሁለት ሰው እንደምንም የምትበቃ አልጋ ላይ ተጣበን አደርን::  እኔ በጣም በጠዋት በመነሳትና ወደ ቤቴ በመሄድ ራሴ አልጋ ላይ መተኛቴን ቀጥዬ የነበረብኝን የወገብ ህምም አስታግሼ ና አረፋፍጄ ተነሳሁ:: አሁን ከጠዋቱ አምስት ሰዓት ተኩል ገደማ ይሆናል.....የልደታ ትዝታ..

ጥቅምት 27 ቀን 1986 አ.ም.

ወሳኝ ወቅት

ከአዲሳበባ እረፍት ከተመለስኩ በሁዋላ አንኩዋር የሆነ አጋጣሚ ባይገጥመኝም: የሶስተኛ አመት የምህርት ሂደትና የኔ ሁኔታ በየቀኑ ባይምሮዬ ይመላለስ ነበር:: ሶስተኛ ዓመት ከገባሁ በሁዋላ በራሴ ላይ ያየሁት ተጨባጭ ነገር ለትምህርት ያለኝ ፍላጎት ክፉኛ ማነሱና ይህም በአንዳንድ የፈተና ውጤቶቼ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን ነው:: ከዚህ በፊት በትምህርት ሂወቴ አይቻቸው የማላውቅ የፈተና ውጤቶች ማግኘት ጀመርኩ:: ይህ ሁኔታ አስደንግጦኝ በርትቶ ለማጥናት በመነሳሳት ፈንታ እኔ ግን የበለጠ የትምህርት ፍላጎቴ ቀነሰ:: ያለፉት ቀናት ጅማ ከገባሁ በሁዋላ ለመጀመርያ ጊዜ በገዘፈ ሃሳብ አእሞሮዬ የተፈተነባቸው  ቀናት ነበሩ:: ምክንያቱም ትምህርቴን አቁዋርጬ ረዘም ያለ እረፍት ለማድረግ ጊዜያዊ መልቀቂያ (ዊዝድሮዋል) ለመጠየቅ አስቤ ነበር:: ነገር ግን ይህ በቀላሉ ይሁን ብዬ የማደርገው ነገር አልነበረም:: አእምሮዬ ጉዳዩን ለመፈፀም ቢገፋፋኝም ከፊቴ የተጋረጡ በቂ መልስ የሚሹ ሞራላዊ የህሊና ጥያቄዎች ነበሩ:: ብዙ ነገሮችና ትዝታዎች ወደአእምሮዬ ተመላልሰው ነበር: ባለፉት ቀናት:: ገና የጅጤሳን ግቢ የረገጥኩ ሰሞን በአውቶቡስ ታጭቀው ወደ ጦር ካምፕ ለስልጠና የሄዱት ጮርቃ ነፍሶች ታውሱኝ:: ከዚያም በድንገት እረፍት ለማድረግ በማሰብ ወደ ጅማ አውቶቡስ ተራ የሄድኩ ጊዜ የተመለከትኩት ትዕይንት ታወሰኝ:: ሌሎች ብዙ ሰዎችና ሁኔታዎች ታወሱኝ......እኔ ከነዚህ ሁሉ እሻላለሁ....አልኩ:: ዞሮ ዞሮ ግን ጭንቅላቴ በሀሳብ ውዝግብ ከሚፈነዳ በሚል ባለፈው ሐሙስ ጥቅምት 25 ቀን ዊዝድሮዋል ለማውጣት ማስረጃ ፍለጋ ከዚህ በፊት ሌሎች ተማሪዎች እንዳደረጉት ዶክተር ይልማ ጋ ሄድኩ:: ይህ ሰው ሳይካትሪስት ወይም የስነ አእምሮ ዶክተር  ነው::  ዊዝድሮዋል ለመጠይቅ የተገደድኩበትን ምክንያት ከላይ እንዳስቀመጥኩት ስነግረው ፈፅሞ ሊዋጥለት አልቻለም::  እኔን በማዳመጥ ብዙ ግዜም መውሰድ አልፈለገም:: በቀጥታ መድረኩን እሱ ተቆጣጥሮት የተለያዩ ምክሮች ከመከረኝ በሁዋላ ትምህርቴን እንድቀጥል በጥብቅ አስጠንቅቆ ሸኘኝ::  የምክሩ ጭብጥ እንደሚከተለው ነበር

" ሰው ሁልግዜ እንደነበረ አይሆንም:: የሂወትን እውነታዎች መቀበል አለብን:: በአንድ ወቅት ከብር የነበራቸው: ሁኔታዎች ሁሉ ተስተካክለውላቸው ይኖሩ የነበሩ ታላላቅ ሰዎች በሌላ ግዜ ክብራቸው ተገፎ: ሁኔታዎች አልሳካ ብለዋቸው የሚወድቁበት ግዜ አለ:: አንድ ሰው ውድቀቱንም በፀጋ መቀበል አለበት:: ውድቀት የማይከሰት ነገር አድርጎ መቁጠር የለበትም:: መጥፎ ግዜ በመጣ ቁጥር ከችግር ለመሸሽ የማይሆን ነገር መስራት የለበትም:: ችግርን መጋፈጥ አለበት......"



ምክሩ እውነት ሆነም አልሆነም በዚህ አይነት ትምህርቴ ቀጠለ ማለት ነው.........

Sunday, March 13, 2016

ነሐሴ 1985 አ.ም.

ለእረፍት ወደ አዲስ አበባ ለመሄድ በተዘጋጀሁበት ዋዜማ ምሽት በጅማ ሰማይ ላይ ታንፅባርቅ የነበረችውን ግማሽ ጨረቃ ምን ግዜም አልረሳትም:: ያይኔ ምግብ የሆነች የማታስከፍል ቆንጆ ድፍን ቀይ ጨረቃ..... ለምን እንደሆነ ባላውቅም ከዚህ ትውስታ ጋር ተያይዞ ያሳለፍኩት የሶስተኛ ዓመት የመጀመሪያው ሴሚስተር ጉዞ ውልብ ሲልብኝ በዚህ ውስጥ ደግም እመቤትን አስታወስኩ:: እመቤት አዲስ አበባ ዮሐንስ ቤተክርስትያን አካባቢ ያፈራት መልካም ሴት:: እመቤት ባለፈው ሴሚስተር ከመቼውም ግዜ በላቀ ከኔ: ከአብይና ከመንጌ ጋር: ቅርርብ ጨምራለች:: ብዙ ጊዜ እኛ ወደተሰበሰብንበት ትመጣና በደስታና በሳቅ ትቀላቀላለች:: በቃ ከኛ ጋር መሆን እየተመቻት እንደመጣ መገመት አያዳግትም:: ከተቀላቀለችን በሁዋላ እንደልቧ ታወራለች: ትስቃለች: ትጫወታለች: መራር የሆኑ ቀልዶቻችንን ትቃለዳለች:: አልፎ አልፎም ሚስጥር ታጫውተናለች:: የአብይና መንጌን አላውቅም እኔ ግን ከአህቶቼ በስትቀር ከተቃራኒ ፆታ ጋር አብሮ መዋል መጫወት ስላለመድኩ ነገሩ አዲስ ሆኖብኛል:: ይህን የምለው ግን ሁኔታው ለኔም እንደተመቸኝ ሳልክድ  ነው::

ነሐሴ 19  ቀን ጅማን ለቅቄና ባውቶቡስ ተፈናጥጬ አዲስ አበባ ቤቴ ደንገዝገዝ ሲል ደረስኩ:: አዲስ አበባ በሚሰነፍጥ ቀዝቃዛ አየር ተቀበለችኝ:: እዚህ አሁንም ድረስ ጠዋቱን ሙሉ ይዘንባል:: ከሰዓት ደግሞ ደነናማ ሆኖ በጣም ይቀዘቅዛል:: ውስጥንም ያቀዘቅዛል:: በነገራችን ላይ በዚህ የእረፍት ግዜ ግጥም ለመፃፍ እቅድ አለኝ::

ጳጉሜ 1985 አ.ም.
እነሆ 1985 ሊፈፀም የቀሩት ጥቂት ቀናት ናቸው:: ከዚያ በሁዋዋላ ያበሻው ፀደይ ወር መስከረም ብቅ ይላል:: መስከረምን በእውነት በጣም እወደዋለሁ:: ልጅነቴን የሚያስታውሰኝ ወር ነው:: አደይ አባባን ያስታውሰኛል:: ኩልል ያለ ውሃ የሚፈልቅባቸው ምንጮችንም ያስታውሰኛል:: ሰፈሩ መንደሩ ሁሉ አረንጉዋዴ መሆኑንም አይዘነጋኝም::  ከጉዋደኞቼ ጋር ሆነን በቀለም አይነትና በቁጥር የበዙ ቢራቢሮዎችን  ስናባርር ትዝ ይለኛል....

በወላጆቼ (በኛ) ቤት ውስጥ የዘመን መለወጫን ለማክበር የሚደረገው እንቅስቃሴ ከሌላው ግዜ የበለጠና ቀልቤን የሳበ ነው:: ለምን እንደሆነ አልገባኝም:: ላለፉት ጥቂት ቀናት ቤት ውስጥ የአውራ ዶሮ ድምፅና ኩኩሉ እየሰማሁ ነው:: ከጉዋዳ የሚወጣው የበዓሉ ለት የሚሰራውን ዶሮና ስጋ ወጥ ለማጣፈጥ ተብለው የተዘጋጁ ቅመማ ቅመሞች: በርበሬና ቅቤ ሽታ መቼም ለጉድ ነው:: እየበሰለ ያለ ጠላ ሽታም አልፎ አልፎ በነፋስ መልክ ወደ ሳሎን ቤት ይመጣል::

በነገራችን ላይ የኛ ቤት ማታ ማታ ሞቅ ይላል:: በየቀኑ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት አካባቢ ረዘም ያለ የቡና ስነስርዓት ይጀመራል:: ከእህቶቼ አንዷ ቡናውን የማዘጋጀት ኃላፊነት ትወዳለች:: ከሰል ይቀጣጠላል: ሰፊ ሮሆቦት ሳሎኑ መሃል ላይ ይሰየማል: ጀበና ይመጣል: ቡና ይቆላል: ፈንድሻም ይንዶሾዶሻል:: እጣንና ዑድ ይጨሳል:: በቡናው መሃል እራት ይቀርባል:: የቡናው ስርዓት ቢያንስ ሁለት ሰዓት ያህል የውስዳል:: በመሃል ቀልድ ሳቅ ጨዋታ ይደራል:: የቡናው ስነ ስርዓት ሲጠናቀቅም ቀስ በቀስ ሁሉም ወደየመኝታው ይሄዳል:: አባታችን ብቻ የራድዮኑን ጣቢያ እየቀያየረ የእንግሊዝኛ ወሬ ሲያዳምጥ ሌሊቱን ያጋምሳል:: እኔም ሳሎን ውስጥ ከተዘረጋልኝ ታጣፊ አልጋ ላይ ተንጋልዬ አብሬው በርቀት አዳምጣለሁ.....

Tuesday, March 8, 2016


ሐምሌ 30 ቀን 1985 አ.ም.

 

ባለፈው ሰሞን  አንድ ቆየት ያለ ከእናቴ የተላከ ደብዳቤ ደረሰኝ:: ከተፃፈ አንድ ወር ይሆነዋል:: ደብዳቤው ከመድረሱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ እናቴ ስልክ ደውላ ፈልጋኝ ነበር አሉ:: እንዳጋጣሚ ሆኖ አልተገናኘንም:: የደወለችበት ዋናው ምክንያት በባንክ ቤት በኩል ሃምሳ ብር እንደላከችልኝ ልትነግረኝ ነበር:: ሸጋ ዜና ነው:: ይህንኑ ብር ከባንክ ቤት ከተቀበልኩ በሁዋላ ከመንጌጋ ወደ ጅማ መርካቶ በመሄድ አንድ ጨርቅ ሱሪ በግማሹ ገዛሁ:: በተረፈው ጉዋደኞቼን ሰብስቤ ሻይና የበቆሎ ጥብስ ጋበዝኩበት…..የሄው ነው ያምሳ ብሩ ታሪክ::

 

በዚህ ቀፋፊ የሐምሌ ቀን በትክክል ምን ተሰምቶኝ እንደሆን ለመናገር ባልችልም የሚከተለውን የስንኝ ቁዋጠሮ ግን አሰፈርኩ….

 

ሃሳብ ከሃሳብ ተጋጭቶ አንዳች ነገር ላይፈጥር

እርስ በርሱ ሲተካካ በላይ በላይ ሲደረደር

ሁሉ ነገር ባዶ ሲሆን የማይጠቅም ሲመስል

የሚያስበው ነገር አጥቶ አእምሮ ባየር ሲዋልል

ዓለም ሁሉ ከንቱ ሲሆን የማይረባ

ጭብጥ የሌለው ከቁምነገር የማይገባ

ደስታ ነገር ሳቅ ጨዋታ ጭልጥ ሲል

ባዘኔታ ተለውጦ በቁዘማ ሲጠቃለል

አየር ለጫንቃ ሲከብድ..ወኔ ስፈራርስ ሲናድ

አእምሮ ነገር ሲያሳድድ..አንድም ላያገኝ የሚወደድ

ሁዋላም በራሱ ሲፈርድ..በምንም ሃሳብ ላይጠመድ

እንቅልፍ እልም ብሎ ሲጠፋ

ጭንቀት በምትክ ሲስፋፋ

ከቶ መጥፎ ነው የሚመር

አንድ ቀን ኑሮ ሲደብር

 

ከዚህ የስሜት ጢቅታ በተቃራኒ ደግሞ ሐምሌ መጨረሻ ላይ አየሩ መልካም እየሆነ የመጣ መስሎ ተሰምቶኛል:: ዝናብ ከዘነበ ጠዋት ብቻ ነው:: ከሰአትና ምሽት ላይ አየሩ ቀዝቀዝ ይልና መጠነኛ ነፋስ ሽው.. ሿ ስል ይሰማል::

 

በአሁኑ ሰዓት በጤና ሳይንሱ ግቢ ውስጥ ያሉት የህክምና ተማሪዎች ብቻ ናቸው ማለት እችላለሁ:: ከሁለተኛ ዓመት ላቦራቶሪ ተማሪዎች በስተቀር ሁሉም የዲፕሎማ መረሃ ግብር ተማሪዎች ለእረፍት ወደየመጡበት ሄደዋል:: እኛም ብንሆን ከሁለት ሳምንት በሁዋላ እረፍት እንወጣለን:: ቀሪውን ክረምትና አዲስ አመት እንቁጣጣሽን ከቤተሰቦቻችን ጋር እናሳልፋለን ማለት ነው:: ይህ መቼም እጅግ ደስ የሚል አጋጣሚ ነው:: ተስፋም ነው::  በበኩሌ ለአብዛኞቹ የሶስተኛ ዓመት ትምህርቶችም ሆነ መምህራን ካደረብኝ ብርቱ ጥላቻ የተነሳ እረፍትንም ሆነ ባጠቃላይ ከዚህ አካባቢ ለተወሰነ ግዜ መለየትን ከመጠን ባለፈ ሁኔታ ስሻ ነበር:: ተመስገን ነው:: ለነገሩ የሶስተኛ ዓመት ትምህርቶች ደስ የሚሉ ሊሆኑ ይችላሉ:: ግን የሚያስተምሩት ሰዎች ላይ ቅሬታና የሻከረ ግምት አለኝ:: ለምሳሌ አንዳንዶቹ እንደ ማይክሮባዮሎጂ መምህር ያሉት ሲጀመር ባህሪያቸው አይስማማኝም:: ጠማማ ሆኖ ነው ለኔ የሚታየኝ:: አንዳንዴ እኔ ራሴን መቼ ይሆን መምህር የማመሰግነው? ብዬ እጠይቀዋለሁ:: ችግሩ የኔ ብቻ ይሆን እንዴ? ግን ደግሞ ወደ ሁዋላ ተመልሼ በጣም የምወዳቸውና የማከብራቸውን መምህራኖቼን አስታውስና እፅናናለሁ:: ለምሳሌ የአስራ አንደኛና አስራሁለተኛ ክፍል ፊዚክስ መምህሬ የነበረውን ህንዳዊውን ሚስተር ናየርን መቼም አልረሳውም:: እዚህ ጅጤሳ ፍሬሽማን ሂሳብ ያስተማረኝን ተስፋልደትን እንዲሁም ያለፈው ዓመት አናቶሚ  ፕሮፌሰሬን ግብፃዊውን ሳላህን በልቤ ከፍተኛ ሰፍራ እሰጣቸዋለሁ:: እነዚህን ሰዎች ሁሉ በበኩሌ አንድ የሚያደርጋቸው ሆኔታ አለ እላለሁ:: ሁሉም የሚያስተምሩትን ትምህርት እጅግ አዋቂዎች: በስራቸው ታታሪዎችና ዘወትር ለሌሎች ቀና አሳቢዎች ነበሩ….

Sunday, January 31, 2016


ሐምሌ 1 ቀን 1985 አ.ም  ከምሽቱ 5 ሰዓት ከ 40 ደቂቃ
ባለፈው ሰኔ መጨረሻ ላይ በዋለው ቅዳሜ: በ 1983 አ.ም አብረውን ትምህርታቸውን ጀምረው የነበሩ የዲፕሎማ መረሃ ግብር ተማሪዎች ሁሉ ተመረቁ:: አንዳንዶቹ የቅርብ ጉዋደኞቻችን ነበሩ:: ስለዚህም ከነሱጋ በመለያየታችን ሆድ ባሰን:: ሰሞኑንም ጉዋዛቸውን ሽክፈው ግቢውን እየለቀቁ ነው......

በዚህ ቀዝቃዛ የክረምት ምሽት ላይ የተለመደውና በተደጋጋሚ ከመከሰቱ የተነሳ እንደወንድም ወይም እህት የተላመድኩት የኤሌትሪክ ኃይል መቁዋረጥ ተከስቶ ስለነበር ማጥናትና ማንበብ አይቻልም ነበር:: እሰይ!!! ስለዚህም በዚህ ትምህርታቸውን በትጋት ለሚከታተሉ መጥፎ ለኔ ግን ሸጋ በሆነ አጋጣሚ ከእመቤትና ፅጌረዳ ጋር ረዘም ያለ የእግር ጉዞ እያደረግን ተናፈስን:: አየሩ መቸም ቀዝቀዝ ያለ ቢሆንም ርጋታ የተላበሰ እንዲሁም ባፍንጫና ባፍ ሲምጉት የሆነ ደስ የሚል ነገር ይዞ ወደውስጥ የሚገባ ስነበር ተመችቶኛል:: ከሴቶቹ እንደተለያየሁ አራቱን ጉዋደኞቼንና የመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼን አብይ: መንግስቱ: ሚሊዮንና አምሳሉን አገኘሁዋቸው:: ከቅርብ ግዜ ወዲህ በተደጋጋሚ እንደምናደርገው ዛሬም ወደ ግሪን ሆቴል ሄደን እየጣንና እየተጨዋወትን አመሸን: ኡፍፍፍ...በቃ በጣም ነው ደስ ያለኝ:: እኔ ትምህርት ሳይሆን የሄን ነው የምፈልገው:: ከጉዋደኛጋ መሳቅ: መጫወት: መቦለት: ማውራት:መቃለድ: መቀለድ: እንደገና መሳቅ........ ወደ ጤና ሳይንሱ ስንመለስ የኤሌትሪክ ኃይል ወደቀድሞ ሁኔታው ተመልሶ ስለነበር አንዳንድ የጥናትና ፅሁፍ ግልበጣ ሥራ ላይ የተሰማሩ ግለ-ተማሪዎችን ማየት ይቻል ነበር::

ሐምሌ 3 ቀን 1985 አ.ም 
ዛሬ ጠንከር ያለ የሐምሌ ዝናብ አረንጉዋዴይቱን ጅማን ደበደባት:: ሐምሌ ሐምሌነቱን ለጅማ አሳወቃት:: መጣሁ: ያዥ እንግዲህ! አላት:: ጅማም ይህን ተቀብላ ክረምት ክረምት መሽተት ጀመረች:: ይበልጥ አረንጉዋዴ ሆነች::በየቦታው እሸት በቆሎ መታየት ጀመረ:: ሻይ የሚጠጣ በረከተ:: ወፍራም ልብሶች ተማሪዎች ላይ ፊጥ ብለው ይታዮ ጀመር:: የቤተ መፅሀፍቱ ሙቀት መቀነሻ ቬንትሌተሮች ስራቸውን አቆሙ:: ስለዚህም ቤተመፅሃፍቱ ውስጥ የርምጃና የመፅሀፍ ገለጣ ድምፆች በቬንትሌተሮቹ ዝዝ...ዝታ መሸፈናቸው ቀርቶ ይሰሙ ጀመር:: ጠዋትም ማታም አየሩ መቀዝቀዝ ጀመረ..........

እንደ አምናው የፊዚዮሎጂ ትምህርት በአንድ መስጠሊ ግብፃዊ መምህር የተነሳ ሊደብረኝ የሚሞክረውን የማይክሮባዮሎጂ ትምህርት እንዴት አድርጌ ቀልቤን እንደምሰጠው ግራ ገብቶኛል:: ሰውየው በጭራሽ አልጣመኝም:: ነካ ነካ ነው የማስተማር ዘዴው:: ከትምህርቱ በተጉዋዳኝ ከፍል ውስጥ በላይበላዩ ሲጃራ ያጨሳል::: እያንዳንዱን ሲጃራ አጭሶ ሲጨርስ እሳቱን የጫማው ሶል ላይ ያጠፋና ቁሩውን በመስኮት ወደውጭ ከወረወረ በሁዋላ ከያዘው ባኮ ውስጥ ሌላ አውጥቶ በላይተር ይለኩሳል:: ከዚህ በፊት አይቼ የማላውቀው ነገር ነው::

ባጠቃላይ ከሁለተኛ ዓመት ይልቅ የሻላል ብዬ የተማመንኩበት የሶስተኛ ዓመት ትምህርት ይባስ ብሎ ደረቅና የማይስብ እየሆነብኝ ነው::

ሐምሌ 5 ቀን 1985 አ.ም 

እኔና ጉዋደኛዬ ቤተማርያም ዛሬ ምሽት ላይ ተአምር በመሰለ ሁኔታ ከሌባ ጡጫና ዝርፊያ አመለጥን:: ነገሩ ባጭሩ እንዲህ ነው:: እኔና ቤተማርያም የዛሬውን የሌክቸር ሆልና የላይብረሪ ጥናታችንን አጠናቀንና አንድ ላይ ሆነን ወደ ዶርማችን ስንመለስ ወደ ዋይት ሃውስ ህንፃ የሚያመራው ቀጭን መንገድ ላይ በግምት ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ 45 ላይ ሁለት ሰውነታቸው ገዘፍ ያሉ ሰዎች ከፊትለፊታችን ወደኛ አቅጣጫ እየተራመዱ አለፉን:: ጨዋታ ይዘን ስለበር አላስተዋልናቸውም:: ሰላሳ ሰኮንድም ያህል ሳይቆይ ከበስተጀርባችን ከፍተኛ ጩኸት ሰማንና ፊታችንን ወደሁዋላ በማዞር ባለንበት ቀጥ ብለን ቆምን:: ወዲያውኑ ከየአቅጣጫው የጤና ሳይንሱ ዘበኞችና ሌሎች ተማሪዎች ወደ ተጮኸበት አቅጣጫ ሲሮጡ አየናቸው:: በትክክል እኛን አልፈው የሄዱት ግዙፍ ሰዎች ሌቦች ነበሩ ማለት ነው! እኔ በበኩሌ ካለሁበት ቆሜ ሌቦቹ ወደ በጨለማ ወደተሸፈነው ጫካው ውስጥ እየሮጡ ሲጠፉ ይታየኝ ነበር:: ማንም የተከተላቸው የለም: ያ አደጋ አለውና:: እኔና ቤተማርያም ከሁዋላችን የነበሩትና በሌቦች ጥቃት የተሰነዘረባቸው ተማሪዎች ባይኖሩ ኖሮ የነሱ እጣ ፈንታ የኛ ይሆን እንደነበር በማሰብ ተሸማቀቅን...ኡ

Thursday, January 21, 2016

ግንቦት መጀመሪያ  1985 አ.ም.

ከመጋቢት 7 አስከ ሚያዚያ አጋማሽ አዲሳበባ በተሰቦቼ ጋር ያሳለፍኩትን አረፍት አጠናቅቄ ወደ ዉዷ ጅጤሳ ተመለስኩ:: የሶስተኛ አመት ትምህርቴንም ጀመርኩ::
አጠቃላይ በሆነ እይታ የዚህን አመት ጅምር ብዙም ደስ የሚል ወይም የሚስብ ነገር አጣሁበት:: ዓመቱ ስሙ PC-2 (ፒሲ ቱ) ይባላል:: ትምህርቶቹ በአይነትና በብዛት ከፒሲ-ዋን ትምህርቶች የሚልቁ  ሲሆን በርካታ ከህክምና ጋር በቀጥታ እንዴት አንደሚገናኝኙ ያልገቡኝ ትምህርቶችንም ያካትታል:: ከህክምና ጋር በቀጥታ የሚገናኙትበግብፆች የሚሰጡን እንደነፓቶሎጂና ፋርማኮሎጂ ያሉት የሚስቡ ቢሆንም ተነበው ለመታወስ ሃይልና ጥረት የሚጠይቁ ይመስላል:: ባለፈው እራሴን ለመግለጽ አንደሞከርኩት የንባብ ሀይልና ጥረት አኔ ዘንድ ያሉ ነገሮች አይደሉም::

ከላይ ከህክምና ጋር የማይገናኙ ያልኩዋቸውን ትምህርቶች የሚያስተምሩን መምህራን በሙሉ አበሾት ሲሆኑ ሀኪም አለመሆን ብቻ ሳይሆን ብዙዎቹ አጅግ በጣም በርካታ ሃሳቦችን በበርካታ ትራንስፓረንት ሺቶች ላይ አስፍረው ነው ወደ ሌክቸር ሆል የሚመጡት:: ወደ ክፍሉ እንደገቡ የትራንስፓረንት ሺት ማስቀመጫ ፕሮጀክተር ላይ የመጀመሪያውን ሺት ያኖሩና ጽሁፉ ከሚንጸባረቅበት ነጭ ጨርቅ ላይ አይናቸውን ተክለው እንዲሁም በከፊል ለኛ ለታዳሚዎቹ ጀርባቸውን ሰጥተው መናገር ይጀምራሉ:: ከዚያም አንዱን ትራንስፓረንት ሺት ሲያነሱና ሌላኛውን ሲያስቀምጡ ብሎም ሲናገሩ ቆይተው ክፍሉን ለቀው ይወጣሉ:: የዚህ ኣይነቱ ሂደት ድምር ውጤት ትምህርት ነው ለማለት ይክብደኛል:: ይልቅስ አኔና ሌሎች ብዙ ፒሲ-ቱ ተማሪዎችን ሰነፍ: የደነዘዝንና: የትምህርት ጥላቻ ያለን እንድንሆን አየገፋፋን ነው:: እውነት ለመናገር ሁላችንም እጅግ ከባድ የሚባለውን ፒሲዋንን አልፈን የመጣን ስለሆንን ፒሲ- ላይ ዘና ማለት እንጂ መጨነቅ ምናምን ገለ-መለ አንፈልግም:: እነዚህ ህክምና አልቦ ትምህርቶች ሲታከሉ ደግሞ የሚሆነውን ለማሰብ አይከብድም:: አኔና ጓደኞቼ እንደዚህ አይነት ትምህርቶች የሚሰጡበት ክፍለ ግዜ ላይ ክፍል አካባቢ አለመገኘትን እንደ ፋሽን ከያዝነው ቆየን....


ግንቦት 14 ቀን 1985 አ.ም.

ምናብ
ዛሬ ለምን አንደሆነ በቅጡ ባይገባኝም ከወትሮው እጅግ በተለየ ሁኔታ በዝምታ ነው የዋልኩት:: በቃ ዝም ማለት አማረኝ:: ከሰዎች ጋር ከመነጋገር ይልቅ በውስጤ የማስበውን ሀሳብ ማስታመም ፈልግሁ:: ይህ መቼም ከባድ ነው:: ምክንያቱም ሰዎች በውስጤ የማስበውን ስለማይረዱ መንገድ ላይም ሆነ ሌላ ቦታ ስንገናኝ በማነጋገር የብቸኝነቴን አጥር በርቅሰው ይገባሉ:: ዝም ማለት የፈግሁበትን ምክንያት ጠረጠርኩ: ምናልባት ኪሴ ባዶ በመሆኑ ይሆናል:: ይህ ግን በተደጋጋሚ እንደውም ያለማቁዋረጥ የሚከሰት ስለሆነ አንዴት ዝም ያስብለኛል? አንግዲህ የእጦት መደጋገም: ማድረግ አለመቻልን በማሳሰብ ልቤን አስከፍቶት ይሆናል:: አውነቱን ለመናገር ባሁኑ ሰኣት የመግዛት አቅሜ እሮብና ቅዳሜ ለጫማ ማስጠረጊያ ከማውላቸው ሁለት የምሳ ላይ ዳቦዎች የዘለለ አይደለም፥:: ባያሳፍርም ቅስም ያጣምማል:: በቃ በረዥሙ ከፋኝ:: የመኖር ጉጉቴ ባይቀንስም አንዳንድ ትምህርት ነክ ነገሮችን ለመስራት የሚያስችል ጉልበት ኣጣሁ::ተፈጥሮኣዊ ባህሪዬ የነበረው ሌክቸር ማዳመጥ ራሱ ሃይል የሚጠይቅ ሆነብኝ:: መጻፍማ አይታሰብም:: ብቻ ባጠቃላይ አእምሮዬ ንቃት ሰውነቴ ደግሞ ብርታት ጎደለው:: ተደጋጋሚ የኪስ ባዶነት በፈጠረው መከፋት የተነሳ::ግን አኔ ብቻ ነኝ አንዴ ኪሰ ባዶ የሆነ? ኣይመስለኝም:: ክርስትያን አንደመሆኔ መጠን በእግዚኣብሄር ተስፋ ማድረግ እንደሚጠበቅብኝ ባውቅም ይህን ስሜት ግን አሁን ልቀዳጀው አልቻልኩም:: አንዳውም መንፈሳዊ ሁኔታ ከልቤ ጭራሽ ጠፋ:: አሁን አኔ የማስበው የዚህን ኣለም ተጨባጭ ሁኔታ አንጂ በእግዚኣብሄር አንድ ነገር ይሆናል የሚል ነገር አይደለም:: ወይኔ ተስፋ ቆረጥኩ ማለት ነው? ወደፊቱ ጨልሞ ታየኝ ማለት ነው? እኮ ኪስ ባዶ በመሆኑ ምክንያት?......ሳልሳሳት አልቀርም:: ልክ ነው አምነት ትዕግስትና ተስፋ ያስፈልገኛል .......