Wednesday, February 4, 2015

የ PC-1 ጅምር

ሚያዚያ አስራምስት ቀን ለፒሲዋን የመጀመሪያ የሆነውን የላቦራቶሪ ከፍለ ጊዜ ጀመርን: ባዮኬምስትሪ:: አቶ ኢሳያስ በተለያዩ መምጠጫ ቱቦዎች (pipettes) ኬሚካሎችን እንዴት ራሳችንን ሳንጎዳ መምጠጥ እንደምንችል አሳየን:: እኔ ታዲያ ባለፈው አመት እንደዚሁ በቱቦ ስመጥ ተምዘግዝጎ አፌ ውስጥ የገባው ምንነቱ ያልታወቀ ኬሚካል ትዝ አለኝ:: ለካ መምጠጥም ትምህርት አለው! በክፍለ ጊዜው ብዙም አልረካሁም:: ምክንያቱም ብዙ የመለኪያ ጠርሙሶች ተበላሽተው ስለነበር በተረፉት ደህና ጠርሙሶች ዙሪያ የተማሪዎች ሽሚያ ነበር:: እኔ ደሞ ሽሚያ ፈፅሞ አይመቸኝም:: ተሰብስበን ስንሰራ እንጋፋለን:: ከስብስቡ ወደሁዋላ ቆሞ አስረጂው የሚለውን ለመስማት አዳጋች ነው.....

ከአራት ቀናት በፊት የትንሣዔ በዓል ዋለ:: በዚህ ቀን እኔ: አባይ; አምሳሉ; መንግሥቱና አያሌው ወይዘሮ አልማዝ ቤት ሄደን ነበር:: ወይዘሮ አልማዝና ቤተሰባቸው በአባይ የተነሳ የምናውቃቸው በጣም ጥሩና ለኛም መልካም አመለካከት ያላቸው ሰዎች ናቸው:: እኛም ዓመት ባል በሆነ ጊዜ እየሄድን እንኩዋን አደረሳችሁ ብለናቸውና ከበቂ በላይ ተስተናግደን እንመለሳለን:: የዚህኛው ፋሲካም ለት እንደተለመደው ነበር:: በጠዋት ወይዘሮ አልማዝ ቤት ስንደርስ እንኩዋን አደረሳችሁ ከሚለው የዓመት ባል ቃላት ልውውጥ ቀጥሎ የማስታውሰው በያይነቱ የቀረበልንን ምግብ ነው:: እጅ የሚያስቆረጥም ቀይና አልጫ ዶሮ ወጥ ከአይብ ጋር ተመግበን አብረው የቀረቡልንን አጥንቶች ቅርጥፍጥፍ አረግናቸው:: የፒሲዋን ትምህርት ግብፆቹ ጅማ በመድረሳቸው መጀመሩ ስለማይቀር በዚህ ዓመት ተረጋግተን የምናከብረው የመጨረሻው ዓመት ባል ፋሲካ ሆነ:: ወይዘሮ አልማዝ ቤት መመገብ ብቻ ሳይሆን ጠላ እየጠጣንና እየተጫወትን ለሶስት ሰዓታት ያህል ቆየን:: ከቴፕ ረኮርደሩም በሚወጡት የአስቴር ከበደ ጣዕም ያላቸው ሙዚቃዎች ተዝናናን:: ልይዘው ብሞክር ልጨብጠው በጥር......ለካስ በሀስብ ነው አወይ የኔ ነገር.....

የሁለተኛ ዓመት ትምህርታችንን በትክክል የጀመርነው ሚያዚያ አስራ ዘጠኝ ቀን ነው ማለት ይቻላል:: የፋሲካ ማግስት ሰኞ እለት በግብፆች:: ፕሮፈሰር ሳላህ ና ባለቤቱን ተዋወቅናቸው:: ሁለቱም አናቶሚና እምብርዮሎጂ በጋራ እንደሚያስተምሩን ፕሮፌሰር ሳላህ ነገረን:: የሚናገሩት እንግሊዝኛ የአረብኛ አክሰንት ቢኖረውም ለመረዳት ያማያስቸግር በመሆኑ ደስ ብሎኛል:: ፕሮፌሰር ሳላህ አግባቡና ሁኔታው ባጠቃላይ ተመችቶኛል:: የሂስቶሎጂ መምህራችንንም ተዋወቅናቸው:: ጠና ያሉ ሰው ሲሆኑ መሐመድ አብደልማሰን ይሰኛሉ::


ማክሰኞ ሚያዚያ ሃያአንድ ቀን ለመጀመሪያ ጊዜ የምንማርባቸውን አራት ሬሶች(cadavers) አየናቸው:: በሰፊው የአናቶሚ ላቦራቶሪ ውስጥ ከጡብ በተሰሩ አልጋዎች ላይ በፀጥታ ተጋድመዋል:: ትክክለኛ የሞቱ ሰዎች ናቸው:: ለምን እንደሆነ ባላውቅም ምንም አልደነገጥኩም:: ሶስቱ ወንዶች ሲሆኑ አንዱዋ ሴት ናት:: ፕሮፌሰር ሳላህ እያመላከተን ቆዳቸውን መቅደድ ጀመርን:: እኔም በቀደዳው (dissection) ዋና ተሳታፊ ነበርኩ..........

1 comment:

  1. ሣሚ፡ እትዬ አልማዝ ቤት እናንተ ሳትቀድሙን ለመድረስ ብዙ እንጥር ነበር፤ ግን ምን ያደርጋል አባይ ኑሮውን እዚያው ያደረገ ይመስል እሱን መቅደም አንችልም ነበር….

    ReplyDelete