Friday, March 31, 2017



መስከረም  26 ቀን 1988 አ.ም. ቅዳሜ ጠዋት

ህልሜ

በሠርጀሪ ፈተና መቃረብ የተነሳ ሰሞኑን ከመተኛቴ በፊት የእንቅልፍ ኪኒን (diazepam) እወስዳለሁ:: ታዲያ ለሽ ብዬ ነው የምተኛው:: እኔ ብቻ ሳልሆን ቁጥራቸው ቀላል የማይሰኝ ባልንጀሮቼ ያለሱ እንቅልፍ እንደማይወስዳቸው ውስጥ ውስጡን ሰምቻለሁ:: ብቻ ይህ የአደባባይ ጉዳይ አይደለም::

ታዲያ በእንቅልፍ ክኒኑ ይሁን ወይም በሌላ ምክንያት ትናንት ሌሊት ለዛሬ ሰፋ ያለና የሚገርም አይነት ሕልም ታየኝ:: የህልሙን እያንዳንዱን ድርጊት ቁልጭ ባለ መልኩ በማስታወሴ ነው ይበልጥ የተገረምኩት....

የቀዶ ጥገና ዲፓርትመንት ኃላፊ የሆነው ዶክተር አለምሰገድ ሌክቸር እየሰጠን ነበር:: የነበርንበት ክፍል ግን ከወትሮው ሌክቸር ሆል የተለየ ነበር:: ሴሚናር ከምናደርግባቸውም ክፍሎች የተለየ ነበር:: ከኔ ቡድን (group) የነበርኩት እኔ ብቻ ነኝ:: ሌሎቹ የት እንደነበሩ ትዝ አይለኝም:: የሆነ ሰው ዶክተር አለምሰገድን ውጭ ቆሞ እየጠበቀው ነበር:: ስለዚህም ዶክተር አለምሰገድ ሌክቸሩን ለማሳጠር በፍጥነት እየተናገረ ነበር:: በእጁ የሲጋራ መለኮሻ ላይተር ይዞ ነበር:: ድንገት ግልፅ ባልሆነልኝ ምክንያት ላይተሩን ለኮሰው:: በዚያው ቅፅበት ከላይተሩ ጫፍ የሚስፋፋ ነጭ ሰማያዊ ጭስ መውጣት ጀመረ:: እኔ ካርቦን ሞኖክሳይድ ነው ብዬ አሰብኩ:: ወይም ሌላ ለሂወት የሚያሰጋ ኬሚካል መሰለኝ:: ክፍሉ ውስጥ የነበረ ተማሪ በሙሉ በያቅጣጫው ሂወቱን ለማትረፍ መራወጥ ጀመረ:: አንዳንዶቹን በጭሱ ታፍነው የክፍሉ ወለል ላይ ሲወድቁ ተመለከትኩ:: ዶክተር አለምሰገድ የት እንደደረሰ አላውቅም:: እኔም ራሴ ትንፋሽ የማጠር ስሜት ይሰማኝ ጀመር::  ባለሁበት ድካምና ጡንቻዎቼ ሲዝሉ ተሰማኝ:: ከየት እንደመጣ ያላወኩት አንድ ሕፃን ልጅ ጋር ከክፍሉ ለመውጣት የምንችለውን ያህል ተፍጨርጭረን መጨረሻ ላይ ተስካልንና ወጣን:: ከዚያም ሩጫዬን ከልጁጋ አብሬ ቀጠልኩ:: ከክፍሉ እንደወጣን ከፊት ለፊታችን ያጋጠመን በረጃጅም የእህል ማሳ ነበር:: ወደማሳው እየሮጥን ገባንበትና በውስጡም ሁነን ሩጫችንን ቀጠልን:: በማሳው የወድያኛ ጥግ ደርሼ አልፌው ስወጣ አብሮኝ የነበረው ልጅ የለም: ብቻዬን ነበርኩ:: ከፊት ለፊቴ መንደር አየሁ:: በአንድ አይነት ሁኔታ የተሰሩ ቤቶች አየሁ::  ቤቶቹ ነጫጮች ሲሆኑ በልጅኔቴ የተማርኩበት ቅዱሥ ጳውሎስ ትምህርት ቤት ግቢ ውስጥ ቀሳውስት ይኖሩባቸው የነበሩ ቤቶችን ይመስላሉ:: ወደቤቶቹ አቅጣጫ እያመራሁ ሳለ አንዲት ኮረዳ በድንገት መንገዱ ላይ  ብቅ ብላ አናገረችኝ:: እኔም በሌክቸር ሆሉ ውስጥ የተፈጠርውን ነገርኩዋት:: እርሱዋም ለደህንነቴ በማሰብ አዳሬን በመንደሩ እንዳደርግ መከረችኝ:: ይህን ካለችኝ በሁዋላ ወዴት እንደሄደች አላውቅም:: እኔ ግን ርምጃዬን ቀጠልኩ:: በመንደሩ ውስጥ ስጉዋዝ በመንገዱ ግራና ቀኝ ትልልቅ አለቶችን የሚፈልጡና የሚጠርቡ ሰዎችን አየሁኝ:: ካለሁበት ቆሜ ወደፊትለፊቴ  ስመለከት በርቀት የረጃጅም ህንፃዎች ጫፎች አየሁ:: ጂማ እንደነዚህ አይንት ፎቆች አይቼ አላውቅም:: ካለሁበት ወደየት እንዳመራሁ ትዝ አየለኝም ግን ሕልሙ እዚያ ላይ አለቀ...........


Tuesday, March 14, 2017


መስከረም 12 1988 አ.ም.

ዛሬ በተማሪዎች ቴሌቪዥን መመልከቻ አዳራሽ ውስጥ “No Place to Hide” የተሰኘው ፊልም ሲታይ እኔም ታደምኩ:: እጅግ የወደድኩት ፊልም ነው:: በልቤ ውስጥ ካለው ነገር ጋ የሚሄድ ጠንካራ ትርጉም አገኘሁበት:: በፊልሙ ውስጥ ያለው ዋና ገፀ ባህሪ በኔ ሚዛን እጅግ መልካም እንዲሁም እውነተኛ: እውነትን ለመታደግ ብሎም ሕግን ለማስከበር የቆመ ስለነበር ወደድኩት::



መስከረም 13 1988 አ.ም. - ራሴን ሳክም

አልፎ አልፎ እንደሚያደርገኝ ዛሬ ደብሮኝ ነበር:: ቀላል ድብርት አይደለም:: ትልቅ የሆነ ድብርት ከነጉዋዙ:: የመሰላቸት ስሜት የገነነበትና በራስ የመተማመን ስሜት ጥቂት የሆነበት:: “የፍልስፍና ሙድ” ውስጥ ነበርኩ:: አለማችን እግዚአብሔር ቆንጆ አድርጎ ቢፈጥራትም በዘመንና በሰው ልጆች ትብብር ቆሽሻ ታየችኝ:: የራሴን ምንነትና በዚህ የቆሸሸ ዓለም ላይ ያለኝን ቦታ ለራሴ ጠየቅሁ:: ራሴን የሆነ ቦታ መመደብ ፈለግሁ ግን ቦታ አጣሁ:: ያለማቁዋረጥ እንቶፈንቶ አሰብኩ:: ለቅፅበት ፍርሃት ውስጥ ገባሁና ወጣሁ:: የያዝኩት ሕክምና ትምህርት ዳግም ከመቸውም የበለጠ ከብዶ ታየኝ:: ተስፋ መቁረጥ ጀምሬ ተስፋ መቁረጤ ራሱ አስፈራኝና ተውኩት::በመፅሐፍ ቅዱስና በታገል ሰይፉ ግጥም ላይ ያነበኩትን የእምባቆምን ለቅሶ አስታውስኩ:: በእግዚአብሔር ታላቅ ተስፋን ለማድረግ ወሰንኩና መተንፈስ ቀጠልኩ........



መስከረም 14 ና 15 1988 አ.ም. - ቻዎ ሰርጀሪ

ዙሩን ለመጨረስ ሶስት ሳምንት ሲቀረኝ ቀዶ ጥገና (surgey) ትምህርት በማያሻማ ሁኔታ ሰለቸኝ:: በቃ በግልፅ ለመናገር  ከዚህ በሁዋላ የተንዛዛ (ቦሪንግ) ነው:: ይህ አምና ስፔሻላይዝ አደርግበታለሁ እንዲሁም በቀዳሚነት እወደዋለሁ ያልኩት ፊልድ የኔ እንዳይደለ ጥርት ብሎ ታየኝ....ቻዎ



መስከረም 17 1988 አ.ም. ሐሙስ ጠዋት - መስቀል

ከዛሬው ይልቅ ስለትናንት ማታ ልናገር:: ለኔና ለጉዋደኞቼ ጥሩ ምሽት ነበር:: እኔና እነመንጌ የመስቀል ዋዜማ በመሆኑ እንደተለመደው: ምሽቱን ወጣ ብለን ለማሰለፍ ሳንቲም አሰባሰብን:: ሳንቲም ካላቸው ጉዋደኞቻችን ተበደርን: አሮጌ ልብሶችና ጫማዎች ገበያ ወደን ጆሮ ግንዳቸውን አልን: ከዚያም ወደ ጅማ ከተማ እምብርት ሄድን...ጠለቅን:: በቅርብ የተዋወቁት መሃንዲሱ ጉዋደኛዬ ጌታሁን አብሮን ስለነበር የኔ ደስታ እጥፍ ነበር:: ሌላው ምሽቱን ልዩ ያደረገው ግርማ ሁንዴ ለመጀመሪያ ግዜ ምሽት ላይ እኛን መቀላቀሉ ነው:: እርሱ ደሞ ቀን ላይ አዲስ መጫሚያ ገዝቶ ስለነበር ተመችቶት ነበር:: ብዙ ግዜ እንዳደረግነው ወይን ጠጅ እየጠጣን ደነስን:: ዶርማችን ስንመለስ መንግስቱ ከሌሎቻችን በገዘፈ ሞቅታ ተኝተው የነበሩትን ጉዋደኞቻችንን ቀሰቀሳቸው:: ነገርግን እነሱ መንም ቅር አልተሰኙበትም:: ምክንያቱም መስቀል በተለምዶ የጉራጌ በዓል ነው ስለሚባል .............