Sunday, November 9, 2014

ፈገግታ

በብሩህ አይኖች እይታ 
በአእምሮ ትእዛዝ ይሁንታ 
በጥርስ ድምቀት ሰጭነት 
በጉንጭ ቅላት ፍካት 
በከንፈር ስፋት ጥበት 
በዉፍረትና በቅጥነት
በአይን ዳርቻ መሸብሸብ
ገፅ በደስታ ሲከበብ 
ለተመልካች እይታ መስህብ 
እንደአበባ መአዛ: እንደ አበባ  ልዩ ሽታ 
እንደነፋስ ሽውታ: እንደፀሃይ ብልጭታ 
ፈገግታ!

ክፉን ከደግ: ሴትን ከወንድ 
ጨዋን ከሌባ: ጤነኛን ከእብድ
የረጋውን ከችኩል: አመለቢሱን ካመለኛው
ኡ ኡ ባዩን ከቀማኛው ከዘራፊው 
'ምታግባባ በአንዲት ቅፅበት እይታ 
ለልብ ለጋሽ እርጋታ...
ፈገግታ!

ሰውን የማክበር ምልክቱ: የባልንጀርነት ስሜቱ
የመውደድ ማፍቀር ማስረጃው: የታማኝነት መግለጫው
የንፁህ ልቦና ምስክሩ: የአዲስ ፍቅር ጅምሩ
የወዳጅነት መለያው: የሂወት ምግብ ማጣፈጫው
ፈገግታ...እንደአበባ ልዩ ሽታ: እንደነፋስ ሽውታ 
ለህሊና ሰጭ እርካታ: ከልብ ደራሽ ባንዳፍታ 
የደስታ ምንጭ ያላት መስህብ
ፈገግታ የሂወት ምግብ
ፈገግታ!

በር ይከፈት በፈገግታ 
ለእንግዳ ረዥም ቆይታ 
ለመስተንግዶው ድምቀት ማማር
ለእንግዳ ምቾት ለመፍጠር
ከምግብ መጠጥ በፊት ለማስታወሻ ለትዝታ
ይቅረብ ከልብ እንደልብ : ያልተሰሰተ ፈገግታ 
ፈገግታ!

ሰላም እንደምን አለህ: ሰላም እንደምን አለሽ 
እንደምን አሉልኝ አብዬ: ደህና ውለዋል እማምዬ
እንደምንድኖት ጌታዬ
ሰላም ዋላችሁ ጉዋደኞቼ
በጣም ደህና ነኝ ቤቶቼ
ባልንበት ሁሉ ለሰላምታ 
ይቅደመን ከልብ ፈገግታ!
ፈገግታ!

እግዜር ይስጥልኝ: ጌታ ይባርክህ
ብዙ ያኑርህ ያሳድግህ 
አመስግናለሁ አባትዬ 
መርቄሻለሁ እህትዬ 
ለተቀባይ ዋጋ የለው
ፈገግታዎ ከተለየው 
ለፈገግታ ይኑሩ: በፈገግታም ይናገሩ
መከራ ፊትዎን ይሰውሩ 

ፈገግታ...


መጋቢት 1982 አ.ም. የተፃፈ - በ ሳምሶን ኃይሌ:: ሃሳቡ እንዳለ ቢሆንም ያፃፃፍ ለውጥ ተደርጎበታል:: ከመጀመሪያው ግጥም የሄኛው በመጠን ያንሳል:: የመጀመሪያው ግጥም  ግንቦት 1982 አ.ም. በአዲስ ከተማ  ትምህርት ቤት በተደረገ  የተማሪዎች የግጥም ውድድር ላይ ቀርቦ ሶስተኛ ደረጃ ያገኘ ሲሆን በወቅቱ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቡዋል::

2 comments:

  1. WOW samson betam des yilal, ene zare gena new yegobegnehut yanten Blog. Betam bizu tiztawoch aluh. I love the poem about Fegegta.

    ReplyDelete
  2. WOW samson betam des yilal, ene zare gena new yegobegnehut yanten Blog. Betam bizu tiztawoch aluh. I love the poem about Fegegta.

    ReplyDelete