Sunday, October 4, 2015

አርብ ታህሳስ 2 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 6 ሰዓት

ፒሲዋን የተሰኘው የጅጤሳው ሕክምና ትምህርት ዓመት (ክፍለ ዘመን ብለው ይቀለኛል) ሊጠናቀቅ የቀሩት 5 ሳምንታት ወይም ሰላሳ አምስት ቀናት ብቻ ናቸው:: ይህን ሀቅ ዛሬ በመረዳቴ ከእንቅልፌ ቀስቅሰው “ስማ አንድ ሳምንት ብቻ ቀረ!!!” ያሉኝ ይመስል ክው ብዬ ቀረሁ:: ላለፈው ዓመት ያህል የትምህርት ግዜ በየቀኑ የተለፈለፉ እውቀቶች: ሃሳቦች: መላምቶች: የሰው ልጅ ህልውና ሳይንሶች: አበላሎች: አተነፋፈሶች:  አወላለዶች: አስተሳሰቦች: አጠቃላይ አሰራሮች: ጭንቅላቴ ውስጥ በተዘበራረቀ ሁኔታ ተከምረውና ተጠቅጥቀው የሚገኙ ሲሆን: የተፃፉ ግን ያልተነበቡ ነጥቦች: ፅሁፎች: የተሳሉ ግን በድጋሚ ያልታዩ የአናቶሚ ስዕሎች እንዲሁም የፊዚዮሎጂ: የባዮኬምስትሪ ግራፎች: አልጎሪዝሞች: ሳይክሎች: ሂደቶች: ፍጭቶች: ግኑኝነቶች: ወዘተ.....በበርካታ ደብተሮችና ማስተወሻዎች  ላይ ሰፍረው: በእኔ በሳምሶን መገለጥን እየጠበቁ በተጠንቀቅ ላይ የሚገኙ መስሎ ይሰማኛል:: ለመጨረሻው የፅሁፍም ሆነ የቃል ፈተና በብቃት እቀርብ ዘንድ ፒስዋንን ሀ ብዬ ከጀመርኩበት ከሚያዝያ ወር 1984 አ.ም. ጀምሮ የተስተማርኩትን: በቅንጭላቴ እንዲሁም በደብተሬ ያኖርኩትን ሁልቆ መሳፍርት እውቀት መልክ መልክ ማስያዝ ይጠበቅብኛል:: በዚህ በጠቀስኩት ግንዛቤ ያለምንም ማጋነን ደንግጫለሁ:: በቀላሉ ሀኪም አይኮንም ለካ.......

እሁድ ታህሳስ 4 ቀን 1985 አ.ም. ከምሽቱ 12  ሰዓት ከ 39 ደቂቃ


በዚህ የአእምሮ ውጥንቅጥ ውስጥ ባለሁበት ወቅት አንድ ቆይቶ በጣም ያሳቀኝን ነገር ከጉዋደኛዬ ከአብይ ጋር ፈፀምኩ:: እሱም እንደኔ በፒስዋን መጨረሻ መድረስ የድንጋጤ መንፈስ ውስጥ ሳይገባ አይቀርም:: ዛሬ ቀን ላይ እኔና አብይ ገላችንን ለመታጠብ እኩል አሰብን:: ተገናኝተን ወደገላ መታጠቢያ ቤቱ እየሄድን ሳለ የመሄዱን ሃሳብ ድንገት በመተው ውሃ በባልዲ ሞልተንና ተሸክመን ወደ ማደሪያ ዶርማችን ተመለስን:: ልብሶቻችንን አወላልቀን የዶርሙ መሃል- ለመሃል- መሃል ላይ በመቆም በባልዲ ጭነን ያመጣነውን ቀዝቃዛ ውሃ ገላችን ላይ እያፈሰስን ታጠብን.....ሳሙና ተለቀለቅን: እንደገናም ገላዎቻችን ላይ ውሃ ቸለስን:: ማደሪያ ዶርማችን ውስጥ ማለት ነው:: ሌሎቹ የዶርም ተጋሪዎቻችን ባካባቢው አልነበሩም:: ዶርም ውስጥ ገላችንን ለመታጠብ ያነሳሳንን ምክንያት በትክክል ባላስታውሰውም ና አብይ የሚሰማውን ባላውቅም ያደረግነውን ነገር ለብቻዬ በተደጋጋግሚ እያሰብኩ ከመሳቄ የተነሳ ጭንቀቴ ቀለል እንዳለልኝ ግን እርግጠኛ ነኝ........

No comments:

Post a Comment