Sunday, June 5, 2016

ሰኔ 21 ቀን 1986 አ.ም.

ሀኪም ወደመሆን…

የኔ ዉድ: ያን የሶስተኛ ዓመት መጨረሻ ገደማ የህክምናን ትምህርት ቀጥሎ የማጠናቀቅ ፅኑ ውሳኔ በልቤ ማኖሬን የሚጠቅስ ማስታወሻ ካሰፈርኩበት ቀን በሁዋላ: ምንም ለትውስታ የሚበቃ ክስተት ሳይኖር: ቀናቱ እንዴት እንደሄዱ ሳላውቀው: ራሴን የአራተኛ ዓመት ሕክምና ትምህርት (C-1) መጀመሪያ ሰሞን አገኘሁት:: ለመጀመሪያ ጊዜ ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያዊ በሆኑ ዶክተሮች ብቻ  ሕክምናን የምንማርበት: እውነተኛ የታመመ ሰው የምናነጋግርበት እንዲሁም የምንመረምርበት ዓመት….. ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች ቀልድ አያውቁም:: ኩሩዎች: ቁጡዎችና ግሳፄያቸው የሚያስፈራ ናቸው:: በየጊዜውና በየሁኔታው ይገስፁናል:: በእውነቱ ሐኪምም ቢሆኑ እነዚህ የሚመቹኝ እንደማይሆኑ ግልፅ ነው:: በእርግጥም አልተመቹኝም:: እነሱ ሲገስፁ እኔ ሲጎረብጠኝ: እነሱ ሲገስፁ እኔ ሲጎረብጠኝ: አራተኛ ዓመት በተጀመረ በአንድ ወሩ የተሰጠኝን በሽተኛን አገላብጦ የመመርመር (Physical Exam) ፈተና ሳላልፍ ቀረሁ:: ማለትም የተዘጋጀልኝን በሽተኛ ከበስተጀርባዬ እንደጅብራ ቆሞ ሲያየኝ ለነበረው ሀኪም(ዶ/ር ሳዲቅ) በሚያረካ መልኩ ሳላገላብጠው: ሳልመረምረው ቀረሁ:: መርምሬውም ዶ/ር ሳዲቅ ከኔ ቀድሞ በሽተኛውን መርምሮ ያወቀውን እኔ ሳላውቅ ቀረሁ:: ዶ/ር ሳዲቅ ሀበሻዊ ቁጣን ተቆጣ:: ገነፈለ:: ዘራፍ አለ:: በሽተኛው ብልብና ትንፋሽ ማዳመጫው (stethoscope) የሚሰሙ: ከሳንባዎቹ የሚፈልቁ ቀጫጭን የስትንፋስ ድምፆች (bronchial  breath sounds) ነበሩት ለካ….የሳምባ ምች (Pneumonia) ተጠቂ ነበር::

ከዚህ አጋጣሚ በሁዋላ መንፈሴ ትክክል አልነበረም:: ከማንም ጋር ማውራት አልከጀልኩም:: ብቻ ቀጥታ ወደ ማደሪያዬ በማቅናት: ፊቴን ወደ ግድግዳው አዙሬ አልጋዬ ላይ ተጋደምኩና: የአይኖቼን ቀዳዶች ፈንቅሎ ሊወጣ የሚዳዳውን ንዴት አዘል እምባ ታገልኩት...

No comments:

Post a Comment